በዳግማዊ አፄ ምኒልክ የተመራው የኢትዮጵያ ሕዝብ ወራሪውን የጣሊያን ሠራዊት በዓድዋ ሰንሰለታማ ተራራዎች ድል የነሳበት 123ኛ ዓመት ክብረ በዓል፣ በመላ አገሪቱ ቅዳሜ የካቲት 23 ቀን 2011 ዓ.ም. ተከብሯል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በዳግማዊ ምኒልክ አደባባይ በርካታ የአዲስ አበባና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት በደማቅ ሥነ ሥርዓት የተከበረ ሲሆን፣ በተለይ ወጣቶች በዓድዋ ጀግኖች አለባበስ ክብረ በዓሉን አድምቀውታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ዓርብ የካቲት 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ‹‹…ኢትዮጵያዊያን በዓድዋ በደምና በአጥንት የከፈሉት መስዋዕትነት፣ የዛሬውና የነገው ትውልድ በቅኝ ግዛት ቀንበር ትከሻው ጎብጦና አንገቱን ደፍቶ እንዳይኖር አስችሎታል፡፡ የዓድዋው ድላችን ተኝተንም ነቅተንም በዓለም ፊት ለመቆማችን አባቶቻችን ያቀዳጁን አክሊል ነው…›› ብለዋል፡፡ ‹‹…በዛሬው ዕለት የዘንድሮውን የድል በዓል ስናከብር እንደዚህ ዘመን ነዋሪና እንደ አዲስ ትውልድ፣ በድሉ ውስጥ የተካተተውን ሰምና ወርቅ፣ ሚስጥርና ቅኔ በጥልቀት በመረዳት መሆን ይኖርበታል…›› ሲሉም አክለዋል፡፡ ‹‹…በትክክል ታሪክን ለሚመረምር ትውልድ ዓድዋ ውስጥ ህልውናን አፅንቶ የመኖር፣ ዓድዋ ውስጥ ዲፕሎማሲ፣ ዓድዋ ውስጥ ወታደራዊ ስትራቴጂ፣ ታላቅ ውስጣዊ የሕዝቦች ኅብረትና አንድነት፣ ጥበብና ተግባቦት፣ ፍቅርና መስጠት፣ ክብርና ጀግንነት ሞልቶና ሰፍቶ የነበረ መሆኑን እናያለን…›› ሲሉም የዓድዋን ድል ታላቅነት አመላክተዋል፡፡ የዓድዋ ድልን ከሥነ ጥበብ፣ ከእምነት፣ ከፍልስፍና፣ ከታሪክ፣ ከሴቶች ተሳትፎ፣ ከመሪነት ጥበብ፣ ከአገራዊ አንድነት፣ ከውትድርና ሳይንስ፣ በኢኮኖሚ ራስን ከመቻል፣ ብሎም ከጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ትግልና የታሪክ ፋና ወጊነት ጋር በማስተሳሰር ዓለም አቀፋዊ ሥራ ማከናወን ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡