የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ራሱን ለማደስ ባደረገው ሁሉ አቀፍ ጥረት መሠረታዊ ችግሮቹንና ድክመቶቹን መለየቱን አስታውቋል፡፡ ለመሠረታዊ ለውጥ ትግበራው መነሻ ጥናት ለማድረግም ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ማውጣቱ ሲነገር ቆይቷል፡፡
ይሁን እንጂ ለፌዴሬሽኑ ቅርበት ያላቸው የሪፖርተር ምንጮች እንደሚገልጹት ከሆነ፣ የጥናቱ ምክረ ሐሳቦች ካስቀመጧቸው አካሄዶች ጋር የሚቃረኑ ዕርምጃዎች ከወዲሁ ሥጋት እንደጣሉበትና በዚህም የፌዴሬሽኑ አመራሮች በሁለት ጎራ በሐሳብ እንዲከፈሉ አድርጓል፡፡
የፌዴሬሽኑን አመራሮች በሁለት ጎራ ያሠለፈው አንዱ ምክንያት ወደ ፌዴሬሽኑ የተለያዩ የሥራ ክፍሎች የሚመጡ ሙያተኞችና ኃላፊዎች በጥቆማና በሰዎች የድጋፍ ድምፅ መሆኑ ሲሆን፣ ይህ አሠራር ከዚህ ቀደም የነበረ በመሆኑ ለጥናቱ ውጤትና ከጥናቱ ምክረ ሐሳቦች በኋላም ይህ አሠራር መቀጠሉ ጥናቱ ለምን አስፈለገ? የሚሉ በአንድ ወገን ጥያቄ እንዲያቀርቡ ሲያደርግ፤ በሌላ ወገን ደግሞ ጥናቱ ምንም እንኳን ‹‹ለውጥ›› እንደሚያስፈልግ የማያወላዳ ቢሆንም፣ ጥናቱን በማይጣረስ መልኩ በተቋሙ መቆየት ብቻ ሳይሆን፣ ብቃቱ ያላቸው አንዳንዶቹ ኃላፊዎችና ሙያተኞች በያዙት ኃላፊነት እንዲቆዩ ቢደረግ ክፋቱ ምንድነው? የሚሉ ናቸው ተብሏል፡፡
በአቶ ኢሳያስ ጅራ የሚመራው ኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አዲሱ አመራር፣ ተቋሙ በአዲስ አደረጃጀት መዋቀር ይችል ዘንድ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ከተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ መሥሪያ ቤቶች ከሚገኙ የዘርፉ ሙያተኞች የተውጣጡ የጥናት ኮሚቴ በማዋቀር ከሦስት ወር በላይ በሆቴል እንዲቀመጡ በማድረግ ጥናቱን ማስጠናቱ ይታወሳል፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ምንም እንኳን ለጥናቱ ያወጣውን የገንዘብ መጠን ይፋ ባያደርግም፣ ነገር ግን ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ማድረጉ ሲነገር ቆይቷል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ የምሥረታ ዕድሜ ካላቸው የስፖርት ተቋማት አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ይሁንና ተቋሙ ዕድሜውንና ዘመናዊ እግር ኳስን የሚመጥን ቁመና ሳይኖረው ዛሬ ላይ ደርሷል፡፡ ይባስ ብሎ እንደ ሌሎች የሙያ ዘርፎች ክብር እንደማይሰጠው በሌሎች ተቋማት አገልግለው በጡረታ አልያም በሌላ ምክንያት የሚሰናበቱ ወገኖች የሚሰባሰቡበት ስለመሆኑ ጭምር ባለሙያው አቶ ዘመድኩን ወንድሙ ይናገራሉ፡፡
የእግር ኳሱ አንዱና መሠረታዊ ተብሎ የሚጠቀሰው ችግር ይህ እንደሆነ የሚናገሩት ሙያተኛው፣ አሁን በሥልጣን ላይ የሚገኘው አመራር ኃላፊነቱን በተረከበ ማግስት ቃል ሲገባ የተደመጠው፣ ‹‹ፌዴሬሽኑን የሚመጥን አደረጃጀት እንዲኖረው ማድረግ›› የሚል እንደነበረና አሁን ላይ ደግሞ ‹‹ለውጥ መኖር አለበት፣ የለበትም›› በሚል ክፍፍል ተፈጥሯል መባሉ እንዳስገረማቸው ይናገራሉ፡፡
ፌዴሬሽኑ ጥናቱን መሠረት በማድረግ በአዲስ መልክ ሲዋቀር በዳይሬክተሮች የሚመሩ ሰባት ዲፓርትመንቶች እንደሚኖሩትና ከእነዚህ ውስጥ የጽሕፈት ቤት ኃላፊው ቦታ እንደተጠበቀ፣ ከቴክኒክ ዲፓርትመንቱና ከሕዝብ ግንኙነት ክፍሉ ውጪ ያሉት ክፍሎች የቅጥር ማስታወቂያ ወጥቶባቸው በአዳዲስ ሙያተኞች ሊዋቀሩ እንደሚገባ እየተነገረ ይገኛል፡፡ የፌዴሬሽኑ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ከሞላ ጎደል በዚህ ተስማምተው መለያየታቸውን ጭምር ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡