የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የመሠረተ ድንጋይ የተጣለበት ስምንተኛ ዓመት በኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶች እየተከበረ ነው፡፡
የህዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ብሔራዊ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው፣ በዓሉ ከሚከበርባቸው ልዩ ልዩ ሁነቶች አንዱ ‹‹ዓባይን በሕፃናት አንደበት›› በሚል መርሕ ታዳጊዎች ይሳተፉበታል፡፡
መጋቢት 30 ቀን 2011 ዓ.ም. በሀገር ፍቅር ቴአትር ከ7፡30 ጀምሮ በሚኖረው ዝግጅት፣ ትምህርት ቤቶችን በማሳተፍ በታዳጊዎች የሚዘጋጁ ስለግድቡ ግንባታ ወቅታዊ ሁኔታ ግንዛቤ የሚያስጨብጡና ንቅናቄን የሚፈጥሩ ግጥሞችና መነባንቦች፣ ድራማዎች ይቀርቡበታል፡፡ እንዲሁም በላ-ልበልሃ፣ በታዳጊዎች አነቃቂ ንግግሮችና የብሔረሰቦች ሙዚቃና መዝሙርም የመሰናዶው አካላት ናቸው፡፡
የዘንድሮው ክብረ በዓል መሪ ቃል ‹‹የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድባችን የአንድነታችን ኅብረ ዜማ የለውጣችን ዓርማ›› መሆኑ ታውቋል፡፡
በቤኒሻንጉልና ጉሙዝ ክልል ጉባ በሚባለው ሥፍራ በዓባይ ወንዝ ላይ ለግድቡ ግንባታ የመሠረት ድንጋይ፣ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የተቀመጠው መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም. መሆኑ ይታወሳል፡፡