የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) በሥሩ ከሚያዘጋጃቸው ሻምፒዮናዎች፣ የአፍሪካ አገሮች በውስጥ ሊግ የሚያወዳድሯቸውን ተጨዋቾች ለማበረታታት በሚል የሚያዘጋጀው የአፍሪካ አገሮች ዋንጫ (ቻን) ይጠቀሳል፡፡ ሻምፒዮናው በየሁለት ዓመቱ አንድ ጊዜ በተመረጡ የአፍሪካ አገሮች ሲዘጋጅ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡
ካፍ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ሊያከናውነው ያቀደው የ2020 ሻምፒዮና ግን አስተናጋጇ ኢትዮጵያ ሻምፒዮናውን የሚመጥን የስታዲየሞች ግንባታ ባለመሟላቷ ዕድሉን ለሌሎች አገሮች አሳልፎ መስጠቱን ይፋ አድርጓል፡፡
በኢትዮጵያ በየዓመቱ ሲከበር የቆየውን የብሔር ብሔረሰቦችን በዓል ምክንያት በማድረግ ደረጃቸውን የጠበቁ በርካታ የስታዲየሞች ግንባታ ተከናውኗል፡፡ ይሁንና ፕሮጀክቶቹ ሲታቀዱ “ማን ከማን ያንሳል” በሚል ስሜታዊነት በመሆኑ ፍጻሜያቸው እንዳያምር ሆኖ አንዳንዶቹ የእንሰሶች መዋያ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ ግንባታቸው ባለበት የአገር ውስጥ ውድድሮች በማስተናገድ ላይ ይገኛሉ፡፡ አንዳንዶቹ ስታዲየሞች መሠረታቸው ተጥሎ ግንባታቸው ከተጀመረ ሁለት አሠርታት ሊሞላቸው የተቃረቡ መኖራቸው ትዝብት ያጫረባቸው አስተያየት ሰጪዎች እንዲበረክቱ ማድረጉ አልቀረም፡፡
ይህንኑ ከግምት ያስገባ የሚመስለው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) በሚቀጥለው ዓመት በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ሊያደርገው የነበረውን ሻምፒዮና መሰረዙ በተለይም ለአፍሪካ እግር ኳስ መፈጠር በመነሻነት ለሚጠቀስ አገር የማይመጥን ብቻ ሳይሆን፣ በቀጣይ ተዓማኒነትን የሚያሳጣ ስለመሆኑ ጭምር የሚያምኑ አሉ፡፡
በዚህ ጉዳይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎች እንደሚናገሩት ከሆነ፣ የቀድሞ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራሮች ካፍ በ2020 የሚያዘጋጀውን የአፍሪካ አገሮች ዋንጫ ኢትዮጵያ እንድታሰናዳ ሲጠይቁ ጉዳዩን ለመንግሥት ማሳወቅ ብቻ ሳይሆን መንግሥትም አምኖበት ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ብሔራዊ ፌዴሬሽኑን በማስተዳደር ላይ የሚገኙት አቶ ኢሳያስ ጅራ ይህንኑ ቢጋሩም፣ ቀደም ሲል የቀረበው ጥያቄ በጥናት ሳይሆን፣ በስሜታዊነት ላይ የተመሠረተ መሆኑ ፌዴሬሽኑም ሆነ አገሪቱ አሁን ላጋጠማቸው ተግዳሮት ምክንያት ተደርጎ ሊወሰድ እንደሚገባ ያምናሉ፡፡
አኅጉራዊ ተቋም ካፍ እዚህ ውሳኔ ላይ ከመድረሱ በፊት፣ ዝግጅቱ በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ በተለይ ሻምፒዮናው የሚደረግባቸው ስታዲየሞች ምን እንደሚመስሉ የሚያጠና ቡድን ዓምና ወደ ኢትዮጵያ ልኮ ጉድለቶች እንደነበሩ፣ ዘንድሮ ደግሞ ሁለተኛውን የቴክኒክ ቡድን ልኮ ባለፈው ዓመት ከነበረው ምንም ዓይነት የማስተካከያ ዕርምጃ እንዳልተወሰደ ለካፍ ሪፖርት ማቅረቡ ምንጮች ለሪፖርተር ሲገልጹ ነበር፡፡ ይሁንና ባለፈው ሳምንት ጉዳዩን አስመልክቶ ከሪፖርተር ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉት አቶ ኢሳያስ ጅራ ከመሠረተ ልማቱ መጓተት ጎን ለጎን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ይሁንታ ሰጥተውት የነበረ መሆኑ፣ የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድም (ዶ/ር) የነበረው ነገር እንዲቀጥል ማረጋገጫ እንዳልሰጡ ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል እንደነዚህ የመሰሉ አገራዊ ዝግጅቶች በዋናነት የሚመለከቱት መንግሥታዊ አካሉ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያ ሻምፒዮናውን በበቂ ሁኔታ ማስተናገድ ትችል ዘንድ ካፍ የሚልከውን የማረጋገጫ ሰነድ መፈረም እንደሚጠበቅባት፣ በነበረው ሁኔታ ግን ኢትዮጵያ ሰነዱ ላይ ፊርማዋን እንዳላዋለች ጭምር መግለጻቸው አይዘነጋም፡፡
ካፍ ባለፈው ቅዳሜ ሚያዝያ 5 ቀን 2011 ዓ.ም. ካይሮ ከሚገኘው ጽሕፈት ቤቱ ይፋ ባደረገው ውሳኔ፣ በሚቀጥለው ዓመት በኢትዮጵያ ሊያካሂደው የነበረው የ2020 የአፍሪካ አገሮች ዋንጫ በመሠረተ ልማት አለመሟላት ምክንያት የአዘጋጅነቱም ሚና ለሌሎች የአፍሪካ አገሮች፣ በዋናነት በመጪው ሰኔ የሚካሄደውን የ2019 የአፍሪካ ዋንጫ መስተንግዶ በተመሳሳይ ችግር ለተነጠቀችው ካሜሮን አሳልፎ የሰጠ መሆኑ ጭምር አስታውቋል፡፡