መንግሥት የሚደጉመው ፓልም ዘይት ደረጃ በደረጃ ወደ ሌሎች ፈሳሽ ዘይቶች እንዲቀየር የጤና ሚኒስቴር መጠየቁን፣ የበሽታ መከላከልና መቆጣጠር ዳይሬክቶሬት አስታወቀ፡፡
ከፍተኛ የጤና ችግር ሊያመጣ የሚችለው ፓልም ዘይት ከ90 እስከ 95 በመቶ በድጎማ የሚገባ ሲሆን፣ ይህንን ለመቀየር እንቅስቃሴ መጀመሩን በዳይሬክቶሬቱ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ተቆጣጣሪ ውባዬ ዋለልኝ (ዶ/ር) ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ሚኒስቴሩ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩትና የመድኃኒትና ምግብ ቁጥጥር ባለሥልጣን ያቀረቸውን ጥናቶች ምክረ ሐሳብ መሠረት በማድረግ፣ የፓልም ዘይት በፈሳሽ ዘይቶች እንዲቀየር ለጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ማሳወቁንና ቢሮውም ንግድ ሚኒስቴር መልስ እንዲሰጥ መመርያ መስጠቱን አስረድተዋል፡፡
ጤና ሚኒስቴር ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የላከውን ደብዳቤ አስመልክቶ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ስምና ማኅተም ታክሎበት ለንግድ ሚኒስቴር የተላከው ደብዳቤ እንደሚለው፣ ጤና ሚኒስቴር በገበያ ላይ ያሉ የምግብ ዘይቶች በጤና ላይ ችግር እየፈጠሩ ነው የሚል ምክረ ሐሳብ አቅርቧል፡፡
በአሁኑ ጊዜ እየቀረበ ያለው የፓልም ዘይት ለጤና ተመራጭ ስላልሆነ ደረጃ በደረጃ በሌሎች ለጤና ተስማሚና ተመጣጣኝ ዋጋ ባላቸው ፈሳሽ ዘይቶች (በሱፍ፣ በአኩሪ አተር፣ በሰሊጥ፣ በኑግና በሌሎች) እንዲተኩ ነው ሐሳብ የቀረበው፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ ሲሆን፣ በኢትዮጵያም ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ጫና ተላላፊ ከሆኑት የሚገዳደሩ ሆነዋል፡፡
ተላላፊ ላልሆኑ በሽታዎች ምክንያቱ የአመጋገብ ሥርዓትና የአኗኗር ዘይቤ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥም የምግብ ዘይት አጠቃቀም ተጠቃሽ ነው፡፡
ይህን ችግር ለመቅረፍ የፓልም ዘይትን በሌሎች ፈሳሽ ዘይቶች መተካት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሶ ጤና ሚኒስቴር በጠየቀው መሠረት፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ንግድ ሚኒስቴር ጉዳዩን ገምግሞ የውሳኔ ሐሳብ ለጠቅላይ ሚኒስትር በጽሕፈት ቤት በአጭር ጊዜ እንዲያቀርብ ውሳኔ ተላልፏል፡፡