የቦርዱ ውሳኔ ይጠበቃል
ከተመሠረተ ከሁለት አሠርታት በላይ እንዳስቆጠረ በሚነገርለት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 14 ጊዜ ዋንጫ በማንሳት አንጋፋው የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ በብቸኝነት ይጠቀሳል፡፡ በእንግሊዛዊ አሠልጣኝ ስቴዋርት ሀል እየሠለጠነ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘንድሮ ለዋንጫ ከሚጠበቁት አንዱ ቢሆንም እያስመዘገበ ካለው ውጤት በመነሳት የዋንጫ ህልሙ እያበቃለት ለመሆኑ እያመላከተ ይገኛል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፈው እሑድ ሚያዝያ 4 ቀን 2011 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ስታዲየም በወራጅ ቀጣና ከሚገኘው ደቡብ ፖሊስ ጋር ያደረገው ጨዋታ በአቻ ውጤት ማጠናቀቁን ተከትሎ የቡድኑ ዋና አሠልጣኝ ስቴዋርት ሀል ከኃላፊነታቸው መልቀቅ እንደሚፈልጉ ለክለቡ ጽሕፈት ቤት ደብዳቤ አስገብተዋል፡፡ ጽሕፈት ቤቱም ደብዳቤውን ለቦርድ እንደሚያቀርብና ውሳኔ እንደሚሰጠው ጭምር ገልጿል፡፡
ክለቡ ዘንድሮ 23 ጨዋታዎችን አድርጎ አሥር ጊዜ ሲያሸንፍ፣ ስምንት ጊዜ አቻና አምስት ጊዜ ደግሞ ተሸንፏል፡፡ በእሑዱ ውጤት የተበሳጩት የክለቡ ደጋፊዎችና አመራሮች በእንግሊዛዊ አሠልጣኝ ላይ ተቃውሟቸውን ሲያሰሙ ተደምጠዋል፡፡ አሠልጣኙ ‹‹የልቀቁኝ›› ጥያቄያቸውን ለማቅረብ የተገደዱት በዚህ መነሻነት እንደሆነም እየተነገረ ይገኛል፡፡
በፕሪሚየር ሊግ ከፍተኛ ክፍያ በመፈጸምና የውጪ አሠልጣኞችን በመቅጠር ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡናና በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ለሆነ የፋይናንስ ቀውስ የተዳረገው ደደቢት በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡ ይሁንና አሠልጣኞቹ ቀጣሪዎቻቸውን ለማስደሰት ካልሆነ አቅማቸውንና የኢትዮጵያውያንን ተጫዋቾች ችሎታና አቅም ግምት ውስጥ ያላስገባ መግለጫ ባዥጎደጎዱ ማግስት ሲባረሩ ካልሆነ በእግር ኳሱ አንዳች ለውጥ ሲያመጡ አልታዩም፡፡
በተቃራኒው በአገር ውስጥ አሠልጣኞች የሚሠለጥኑ የክልልና የአዲስ አበባ ቡድኖች የተሻለ ውጤት በማስመዝገብ ለዋንጫ እየተጫወቱ መገኘታቸውን ተከትሎ፣ የውጪዎቹ አሠልጣኞች ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ መግባት መጀመሩ እየተነገረ ይገኛል፡፡