በዋካንዳ ኢትዮጵያ
ሰሞኑን የምርጫ ቦርድ የ2012 ዓ.ም. ምርጫ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እንዲካሄድ ዝግጅት እያደረግኩ ነው ብሏል፡፡ በትይዩም የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የፖለቲካ ተንታኞች፣ ኢትዮጵያና ሕዝቧን አሳቢዎች፣ የቡድንና የግል ጥቅም አሳዳጆች፣ የአገራችን ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ሁሉ በአደባባይና በየጓዳው ቀጣዩ ምርጫ በጊዜው ይደረግ ወይስ ይራዘም? በሚል የመሰላቸውን ሐሳብና አንዳንዴም መግለጫ እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ የምርጫው ጊዜ ለአንዳንዶች የሕገ መንግሥት ጉዳይ፣ ለአንዳንዶች የእውነተኛ ዴሞክራሲ መወለጃ፣ ለሌሎች ሥልጣን ላይ የመውጫ፣ ለሌሎች ደግሞ የምጥ ጣር መጀመርያ ቀን ነው፡፡
እንደ እኔ ከሆነ ግን ምርጫው በጊዜው ይደረግ ወይስ ይራዘም የሚለው ውዝግብ ዋና ጉዳይ ነው ብዬ አላስብም፡፡ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት (የዴሞክራሲ ፍቺው ይኸው ነውና) በእውነት የሚታገሉና የአገራችንን የእስካሁን ምርጫዎች የገመገሙ ሁሉ፣ ምርጫም ሆነ የምርጫው ጊዜ ዋና አጀንዳቸው ነው ብዬ መገመት ይከብደኛል፡፡ ምክንያቱም በአገራችን ኢትዮጵያ ከቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ የተከናወኑና የተራዘሙ ብዙ ምርጫዎች ተደርገው፣ አንዳቸውም የኢትዮጵያን ሕዝብ የሥልጣን ባለቤት እንዳላደረጉት በሚገባ ስለሚያውቁ ነው፡፡ መምረጥ ከዴሞክራሲ መብቶች ውስጥ አንዱ እንጂ በራሱ ዴሞክራሲ አይደለም፡፡
የምርጫ ቦርድ፣ መከላከያው፣ የፀጥታ ተቋማትና የፍትሕ አካላት ከፖለቲካ ቡድን ገለልተኛ የመሆን አስፈላጊነት እንደተጠበቀ ሆኖ ከዚህ በተጨማሪ የሕዝቡ ምርጫ ‹‹ነፃ›› መሆኑን ልናረጋግጥ ይገባል፡፡ የምርጫ ካርድን በሚስጥር በምርጫ ኮሮጆ ውስጥ መክተት ምርጫን ‹‹ነፃ›› አያደርገውም፡፡ እንደዚህ ቢሆን ኖሮ እስካሁን የተደረጉት ምርጫዎች አብዛኞቹ ‹‹ነፃ›› ነበሩ ማለት ይቻል ነበር፡፡ ከቀረቡልን አማራጮች ውስጥ አንዱን ስለመረጥን ‹‹ነፃ›› ምርጫ አደረግን ማለት አይደለም፡፡ ምርጫ ‹‹ነፃ›› የሚሆነው አማራጮቹ ውስጥ የመራጩ ፍላጎት የተካተተ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ይህ እንዲሆን በአማራጮቹ ዝግጅት ውስጥ የመራጮች ተሳትፎ አስፈላጊ ነው፡፡ የስብሰባን አጀንዳ የቀረፀ የስብሰባውን ሒደት ይቆጣጠራል፣ አማራጮችን ያዘጋጀም ምርጫን ይቆጣጠራል፡፡
ለምሳሌ ‹‹ምላስና ሰንበር›› ለመብላት ወደ ምግብ ቤት ሄድን ልበል፡፡ ነገር ግን በምግብ ቤቱ የምግብ ዓይነቶች ዝርዝር ውስጥ ‹‹ዱለት›› እና ሌሎች ምግቦች እንጂ ‹‹ምላስና ሰንበር›› የለም እንበል፡፡ ያለን አማራጭ ወይ ተቀራራቢውን ‹‹ዱለት›› ወይም ሌላ ቀልባችን የወደደውን ማዘዝ፣ አለበለዚያ ትቶ መሄድ ነው፡፡ ምላስና ሰንበር ፈልገን ዱለት ከበላን ምርጫችን ነፃ አይደለም፡፡ ምርጫችን በምግብ ቤቱ የምግብ ዝርዝር ተገድቧልና፡፡ ነገር ግን የምግብ ቤቱ ባለቤት የፈለግነው ምግብ በዝርዝሩ ውስጥ ባይኖርም፣ ጥያቄያችንን ተቀብሎ ሠርቶ ካቀረበልን ምርጫችን ነፃ ይሆናል፡፡
እስካሁን በአገራችን የተደረጉት ምርጫዎች ችግራቸው የአማራጮች አለመኖር ብቻ ሳይሆን፣ አማራጮቹ የተዘጋጁት በተመራጩ በመሆኑ ነው፡፡ አሁንም በርን ግጥም አድርጎ ዘግቶ እኔ፣ መራጭና ምርጫ አንድም ሦስትም ነን እያሉ፣ የተለያዩ አስተሳሰብ ያላቸውን ከሕዝብ ጋር እንዳይገናኙ በክላሽንኮቭ እያስፈራሩ፣ ሕዝብን ‹አንተ አታውቅም እኛ ያልንህን ብቻ ስማ› እያሉ፣ ‹እንትንና እንትን ለድርድር አይቀርቡም፣ እንትንና እንትን ደግሞ በመቃብራችን ላይ ነው› እያሉ ምርጫችን ነፃ ይሆናል ማለት አይቻልም፡፡ ነፃ ምርጫ የሕዝብ አጀንዳ የሚሰማበት እንጂ፣ የፖለቲካ ድርጅቶች አጀንዳ የሚፀድቅበት አይደለም፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶች ሚና የሕዝብ ፍላጎትን ያሟላል የሚሉትን ፕሮግራም መቅረፅ፣ በሕዝብ አጀንዳ ላይ አቋም መውሰድና ሕዝቡ ለሥልጣን ካበቃቸው በቃላቸው መሠረት መተግበር ነው፡፡ ካልተገበሩ በሚቀጥለው ምርጫ የመረጣቸው ሕዝብ ይቀጣቸዋል፡፡
የምንፈልገው ምርጫ የይምሰል ሳይሆን አገራችንን ወደ እውነተኛ ዴሞክራሲያዊነት መቀየሯን አብሳሪ ስለሆነ፣ ሕዝቡ በአማራጮቹ ላይ ወሳኝ ሚና እንዲኖረው ማድረግ ከምርጫ ጊዜ እሰጥ አገባ ሊቀድም ይገባዋል፡፡ የአገራችን የፖለቲካ መዋቅር ካልተቀየረ ምርጫው አንዱን የልሂቅ ቡድን በሌላ ከመተካት በስተቀር ሌላ ፋይዳ አይኖረውም፡፡ ስለዚህ በራቸውን በተቃዋሚዎቻቸውም ሆነ በተፎካካሪዎቻቸው ላይ ክርችም ያደረጉ መክፈት ይኖርባቸዋል፡፡ በጦር መሣርያ የሚያስፈራሩም የጦር መሣሪያቸውን ወርውረው አዕምሯቸውን እንዲታጠቁ ያስፈልጋል፡፡ በመቃብራችን ላይ የሚሉም የእነሱ በሕይወት መኖር እንጂ ሞታቸው ስለማይጠቅመን ይህን እንዲሉ ያደረሳቸውን ለድርድር የማይቀርበውን ሐሳብ በእርጋታ ቢያስደምጡንና ሕዝብን ቢያዳምጡ ይበጃል፡፡
በአጠቃላይ የትኛውንም የፖለቲካ መስመር ይከተሉ ሁሉም ድርጅቶችና ፓርቲዎች በየትኛውም የአገራችን ክፍሎች ከፈለጉት ማኅበረሰብ ጋር ተገናኝተው እንዲወያዩ ማድረግና ሁኔታዎችን ማመቻቸት፣ ከምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ንትርክ ቅድሚያ የሚሰጠው ነው፡፡ ሕዝብ ሁሉ ፖለቲከኛና የፖለቲካ ድርጅቶች አባል ሊሆን አይችልም፡፡ ነገር ግን የሚፈልገውን ያውቃልና ፍላጎቶቹ በአማራጮች ውስጥ እንዲካተቱ ያለ ምንም ገደብ ከሁሉም ጋር የመገናኘትና የመወያየት ሰብዓዊና ሕገ መንግሥታዊ መብቱ ሊከበር ይገባል፡፡ የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት ሙሉ ለሙሉ የሚረጋገጠው በምርጫ ሳይሆን በ‹‹ነፃ›› ምርጫ ነውና፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡