በኦታዋ ማራቶን የኢትዮጵያውያኑ ድል
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በኳታር ዶሃ ለሚዘጋጀው የ2019 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዝቅተኛ መስፈርት (ሚኒማ) የሚያስፈልጋቸውን ርቀቶች ለየ፡፡ ተቋሙ በድረ ገጹ እንዳስታወቀው፣ ርቀቶቹ 10.000 ሜትር በሁለቱም ጾታ፣ 3,000 ሜትር መሰናክል በሁለቱም ጾታ፣ በ1,500 ሜትር ወንዶችና በ800 ሜትር በሁለቱም ጾታ ሲሆን የማጣሪያው ውድድር ደግሞ ሐምሌ 10 ቀን 2011 ዓ.ም. በሆላንድ ሄንግሎ ይከናወናል፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ከሆላንዳዊው የአትሌቶች ማናጀር ሚስተር ጆን ሄርሜንስ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የሚኒማ ማሟያ ውድድር ስለመሆኑ ጭምር ተነግሯል፡፡
ይሁንና አንዳንድ ሙያተኞች ዘንድሮ ይከናወናል ተብሎ የሚጠበቀው 17ኛ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአስተናጋጅነት የተመረጠችው ኳታር ዶሃ የአየር ፀባይዋ ሞቃታማ በመሆኑ አትሌቶች ከወዲሁ ከኳታር ጋር የሚቀራረብ የአየር ፀባይ ወዳላቸው ስፍራዎች ተንቀሳቅሰው መዘጋጀት ያስፈልጋቸዋል የሚል የጸና እምነት እንዳላቸው ይናገራሉ፡፡ ምክንያቱን አስመልክቶ አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ለውድድሩ የሚያስፈልገው ማጣሪያ ከሐምሌ 10 ቀደም ብሎ ቢደረግ ለሻምፒዮናው የሚመጥን ዝግጅት ለማድረግ ስለሚያስችል እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡
በሌላ በኩል ባለፈው እሑድ ግንቦት 18 ቀን በካናዳ ኦታዋ በተዘጋጀው ማራቶን ኢትዮጵያውያኑ እንስቶች ተከታትለው በመግባት ሲያሸንፉ፣ በወንዶች ሁለተኛና ሦስተኛ በመሆን ያጠናቀቁበትን ድል አስመዝግበዋል፡፡ ኬንያዊው አልበርት ኮሪር የርቀቱ አሸናፊ ሆኗል፡፡
የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር ዕውቅና ከሚሰጣቸው የጎዳና ውድድሮች አንዱ በሆነው የኦታዋ ማራቶን በሴቶች ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙት አሸናፊዋ ትዕግስት ግርማ ርቀቱን 2:26:34 አጠናቃ ሲሆን፣ ቤተልሔም ሞገስና እታፈራሁ ተመስገን ደግሞ 2፡27:00 እና 2፡28:44 በመግባት መሆኑ የአይኤኤኤፍ ዘገባ አመልክቷል፡፡ በወንዶች መካከል በተደረገው ተመሳሳይ ውድድር ኬንያዊ አልበርት ኮሪር 2፡08:03 ሲያጠናቅቅ ኢትዮጵያውያኑ አበራ ኩማና ጽዳት አያና 2፡08: 14 እና 2፡08: 53 በመግባት እንደሆነ ጭምር ዘገባው አመላክቷል፡፡