ኢትዮጵያ ተስፋ ያላት አገር ናት ሲባል ለለበጣ የሚነገር ወይም ደግሞ የማይጨበጥ ምኞት የሚገለጽበት ሳይሆን፣ መልካም አጋጣሚዎችን በሚገባ መጠቀም ከተቻለ ተዓምር መሥራት ስለማያቅት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ 110 ሚሊዮን ይሆናል ተብሎ ከሚገመተው የኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ፣ 70 በመቶ ያህሉ ከ30 ዓመት በታች ነው፡፡ ኢትዮጵያ የታዳጊዎችና የወጣቶች አገር መሆኗ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ ከሰላሳ ሚሊዮን በላይ ዜጎች በትምህርት ገበታ ላይ መገኘታቸው በራሱ መታደል ነው፡፡ ሰፊ ለም መሬት፣ ከፍተኛ የሆነ የውኃ ሀብት፣ ተዝቀው የማያልቁ ማዕድናት፣ አስደማሚ የቱሪዝም መስህቦች፣ የተለያዩ የአየር ፀባዮች፣ አስገራሚ መልክዓ ምድሮችና ሌሎች የተፈጥሮ በረከቶች ገና ያልተነኩ ፀጋዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ በረከቶች በላይ ግን እጅግ በጣም የተከበረ አስተዋይና ጨዋ ሕዝብ ያላት ኢትዮጵያ፣ ሠርቶ የሚያሠራ ጠንካራ መንግሥት ካገኘች ደግሞ ለማመን የሚከብድ ብልፅግና ይገኛል፡፡ ኢትዮጵያን የተስፋይቱ ምድር ለማድረግ ግን በዲሲፕሊን የተሞረደ የሥራ ባህል፣ በሞራልና ሥነ ምግባር የተቀረፀ አስተሳሰብና ክፉ ድርጊቶችን የሚፀየፍ የጋራ እሴት ማበጀት የግድ ይላል፡፡ በዚህ መንገድ ለመጓዝ ዝግጁ መሆን ከተቻለ አገር ከረከሱ ድርጊቶች ነፃ ወጥታ፣ የዕድገት ግስጋሴዋን በአስተማማኝነት ለማስቀጠል አይከብድም፡፡
ለአገር መልካም ምኞት ብቻ ሳይሆን በተግባር የሚታይና የሚለካ አስተዋጽኦ ያስፈልጋል፡፡ ከዚያ በፊት ግን ችግሮችን ማውሳት ጠቃሚ ነው፡፡ ችግሮችን ማወቅ የመፍትሔው ግማሽ አካል ነውና፡፡ በአሁኑ ጊዜ ትልቁ ችግር የአገርን ጉዳይ ከጠባብ ቡድናዊና ግላዊ ፍላጎት በታች የማድረግ አባዜ ነው፡፡ የአገርን ህልውና ከፖለቲካ ፓርቲ፣ ከጠባብ ስብስብ፣ ከማይዳሰስና ከማይጨበጥ ርዕዮተ ዓለም፣ ከሥልጣን፣ ከጥቅማ ጥቅምና ከመሳሰሉት ነገሮች በታች ማድረግ የተለመደ ሆኗል፡፡ ሌላው ቀርቶ በአፋቸው ‹ኢትዮጵያ! ኢትዮጵያ!›› የሚሉ አስመሳዮች ጭምር ሸፍጥ ይፈጽማሉ፡፡ በአገርና በሕዝብ ህልውና ላይ የሚቆምሩ እየበዙ ለመምጣታቸው አንዱ ማሳያው፣ የንፁኃንን ሕይወት ማጥፋትና ማፈናቀል የተለመደ ክስተት መሆኑ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በለውጥ ሽግግር ውስጥ ሆና የሕዝቡን የዘመናት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ለመመለስ የሚያስችል ምኅዳር እንዲፈጠር ከማገዝ ይልቅ፣ ግላዊና ቡድናዊ ጥቅሞችን ለማስጠበቅ ሲባል ብቻ በበርካታ ሥፍራዎች ግጭቶች እየተቀሰቀሱ በርካቶች ተገድለው ሦስት ሚሊዮን ንፁኃን ተፈናቅለው ሜዳ ላይ ተጥለዋል፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ የግለሰቦችን ዕለታዊ ፀቦች የብሔር ገጽታ እያላበሱ ከፍተኛ የፀጥታ ሥጋት መፍጠር ተለምዷል፡፡ ለአገር አንዳችም አስተዋጽኦ የሌላቸው ግለሰቦችና ስብስቦች ጠያቂ በማጣታቸው ብቻ የአገር ተስፋ እያጨለሙ ነው፡፡ የአገር ተስፋ በእነዚህ ከንቱዎች ከሚጨልም እነሱን ጨለማ ቢውጣቸው ይሻላል፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ በታሪኩ የሚታወቀው እርስ በርሱ ተደጋግፎ ደግና ክፉ ጊዜያትን ሲያሳልፍ እንጂ፣ አንዳንድ ምግባረ ብልሹዎችና ዘረኞች እንደሚሉት ውስጡ ቁርሾ ኖሮ አያውቅም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምንም ነገር በላይ ቅድሚያ ሲሰጥ የኖረው ለአገሩ ነው፡፡ በጉራዕ፣ በጉንደት፣ በዓድዋ፣ በካራማራ፣ ወዘተ. በመሳሰሉት በወራሪዎች የተቃጡ ጦርነቶችን ሲመክትና ተስፋፊዎችን ሲያሳፍር ነው የኖረው፡፡ ይህ ተምሳሌትነቱ ለዓለም ጥቁር ሕዝቦች መመኪያ እንዳደረገው ታሪክ ይመሰክራል፡፡ በሰላም ጊዜ ደግሞ ያለችውን እየተጎራረሰ፣ አንተ ትብስ አንቺ እየተባባለ፣ ሃይማኖትና ባህል ሳይገድቡት እርስ በርሱ ተጋብቶ እየተዋለደ፣ ሰብዓዊነትን ተጎናፅፎ ባዕዳንን ጭምር እያስተናገደና እያስጠለለ ዘመናትን የተሻገረ ኩሩና አስተዋይ ሕዝብ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን ይህንን ፀጋውን እንደተላበሰ እንደሚገኝ ግጭቶች ሲቀሰቀሱ በሚገባ ታይቷል፡፡ የገዛ ወገኑን ከአጥቂዎች በግልጽ መታደጉ ይህንን ያረጋግጣል፡፡ ይህንን የመሰለ ታሪክ መሥራት የሚችል ሕዝብ በአግባቡ መርቶ ታላቅ መሆን ሲቻል፣ የማይረቡ ተረቶችንና የተዛቡ ታሪኮችን ማመንዠግ ያሳፍራል፡፡ ኢትዮጵያ ታላቅ መሆን የምትችለው ከማይረቡ ድርጊቶች ውስጥ በመውጣት ኃላፊነትን መወጣት ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ያለው ከንቱ ድርጊት ዕርባና ቢስ ነው፡፡
የዘመኑ ትውልድ ዕድለኛ ነው፡፡ ዘመኑ ያፈራቸው የረቀቁ የቴክኖሎጂ መሣሪያዎች ብዙ ነገሮችን እያቀለሉት ነው፡፡ የዘመኑ የዳበረ ዕውቀት የአስተሳሰብ ደረጃውን ከፍ እያደረገ ነው፡፡ ወደ መንደርነት የጠበበችው ዓለም በርካታ ድንቅ ነገሮችን እያቋደሰች ነው፡፡ ራስን ለትምህርት፣ ጥልቅና ሰፊ ለሆነው የዓለም ስጦታ ዝግጁ ማድረግ ከተቻለ በርካታ ትርፍ የሚያስገኙ ጠቀሜታዎች ይገኛሉ፡፡ የማይረቡ ድርጊቶችም ብዙ ስለሆኑ እነሱም ያሳስባሉ፡፡ ማሰብና ማመዛዘን የሚችል አዕምሮ ግን የተሻለውንና የሚጠቅመውን ስለሚመርጥ፣ ለዚህ የታደሉ በሀብትም ሆነ በኑሮ ዘይቤ ታላቅ አገር ይገነባሉ፡፡ ኢትዮጵያ የምትፈልገው በእንዲህ ዓይነቱ ሚዛን ላይ የሚገኙ ልጆቿን ነው፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያ ውስጥ መሽገው ሐሰተኛ ወሬ የሚፈበርኩ፣ ሁሉንም ነገር የተቃርኖ ምንጭ የሚያደርጉ፣ ትልቁን ብሔራዊ ጉዳይ ወደ ጎን እየገፉ የማይረቡ ጉዳዮች ላይ የሚጠመዱ፣ ለብሔራዊ መግባባት ሳይሆን ግጭት ለመቀስቀስ የሚማስኑ፣ ታዳጊውን ትውልድ በዘረኝነት የሚመርዙና ከጎጥ አስተሳሰብ ውስጥ መውጣት የማይፈልጉ ከንቱዎች ለኢትዮጵያ ጥፋት እንጂ ፋይዳ የላቸውም፡፡ እነዚህን ፋይዳ ቢሶች ማሳፈር ከታሪክ ባለ ዕዳነት ነፃ ያወጣል፡፡
ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊት አገር መሆን የምትችለው በሥርዓት መምራትና መመራት ሲቻል ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ለሕግ የበላይነት አጥብቆ መጨነቅ ያስፈልጋል፡፡ የሕግ የበላይነት ሲኖር ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አስተማማኝ የሆነ የሕግ ጥበቃ ያገኛሉ፡፡ ማንም እንዳሻው እየተነሳ የማንንም መብት መጋፋት አይችልም፡፡ የፍርድ ቤቶች ነፃነት ይከበራል፡፡ ፍትሕን እንደ ሸቀጥ ለገበያ ማቅረብ አይቻልም፡፡ ጉልበተኞች እንደፈለጉ የሚፈነጩበት ሜዳ አይኖርም፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት የሚረዱ ተግባራት በሥርዓት ይከናወናሉ፡፡ ምርጫ ነፃ፣ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊና አሳማኝ ሆኖ ይከናወናል፡፡ ሐሳባቸውን በነፃነት መግለጽ የሚፈልጉ ያለ ምንም ከልካይ ይስተናገዳሉ፡፡ ከፖለቲካው ምኅዳር ውስጥ ጠመንጃና ሕገወጥ ድርጊቶች ይወገዳሉ፡፡ ሕዝብ በነፃነት፣ በእኩልነትና በፍትሐዊነት የሚተዳደርበት ሥርዓት እንዲመሠረት የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያን ለሕግ የበላይነት ትኩረት ማድረግ አለባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ተስፋ የሚለመልመው ይህንን ማድረግ ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ይህ ምኞት ዕውን ይሆን ዘንድ ደግሞ የኢትዮጵያ ተስፋ በከንቱዎች መጨለም የለበትም መባል ይኖርበታል!