ስምንት ሰዎች ሞተዋል
በሱዳን አብዮት ተቀስቅሶ የቀድሞ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኦማር አልበሽር ከሥልጣን ከለቀቁ በኋላ፣ መንበሩን የተቆጣጠረው ወታደራዊ መንግሥት በየቀኑ ለተቃውሞ ከሚመጡ ዴሞክራሲ አቀንቃኝ ሱዳናውያን ጋር በፈጠረው ግጭት ስምንት ሰዎች መሞታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ላለፉት አራት ወራት በየዕለቱ በሱዳኗ መዲና ካርቱምና በሌሎች ከተሞች ለተቃውሞ በመውጣት፣ አልበሽር ከሥልጣን እንዲወርዱ ያደረጉት ምሁራን፣ ተማሪዎችና የሕክምና ባለሙያዎች በአልበሽር እግር የተተካውን ጊዜያዊ ወታደራዊ ካውንስል መቃወም ከጀመሩም ወር አልፏል፡፡
ወታደራዊ መንግሥት ይብቃ፣ ምርጫ ተከናውኖ አገሪቷ በሲቪል ትተዳደር በሚል አልበሽር ሥልጣን ከለቀቁ በኋላ የካርቱምንና የሌሎች ከተሞችን ጎዳናዎች ሲያጨናንቁ የከረሙ ተቃዋሚዎች፣ እስካሁን ከነበረው በተለየ መልኩ ከፀጥታ ኃይሎች ጋር ተጋጭተዋል፡፡
በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ሱዳናውያን በመከላከያ ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት ተቃውሞ መግለጽ ከጀመሩ ወር ቢያልፍም፣ ከፀጥታ ኃይሎች ጥይት የተተኮሰውም ባለፈው ሰኞ ነው፡፡ በዚህም ስምንት ሰዎች ሞተዋል፣ በርካቶች ቆስለዋል ተብሏል፡፡
ሱዳን በወታደራዊ ሽግግር ካውንስል መመራት ከጀመረች ወዲህ በተቀሰቀሰ የሰኞው ግጭት የፀጥታ ኃይሎች ስምንት ገድለው በርካታ አቁስለዋል ቢባልም፣ ካውንስሉ ኃይል መጠቀሙን አስተባብሏል፡፡
‹‹የሱዳን ፀጥታ ኃይል በመከላከያ ዋና ቢሮ አቅራቢያ ቁጭ ብለው ተቃውሞ የሚገልጹትን ለመበተን ጥረት አላደረገም፣ ፀጥታ ኃይሉ ለመበተን የሞከረው፣ ከመከላከያ ዋና መሥሪያ ቤት ጥቂት ርቆ በሚገኝ ሥፍራ ሆነው በመቃወም ለነዋሪውም ሥጋት በፈጠሩት ላይ ነው፤›› ሲል በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ መቀመጫውን ያደረገው ስካይ ኒውስ ቴሌቪዥን ጣቢያ የወታደራዊ ሽግግር ካውንስል ቃል አቀባይ ሌተና ጄኔራል ሻምስ አልአዳን ካባሺን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
እንደ ቃል አቀባዩ፣ መከላከያ ሠራዊቱ ሱዳናውያን ቁጭ ብለው ተቃውሞ ከሚገልጹበት ባሻገር ከሚገኝ ሙስናና አሉታዊ ድርጊቶች ይፈጸሙበታል ወደ ሚባል ሥፍራ አቅንቷል፡፡
‹‹ሥፍራው ለነዋሪው ዋና ሥጋት የፈጠረ ነው፡፡ ከነዋሪው ባለፈም ቁጭ ብለው ተቃውሞ ለሚያሰሙትም ቢሆን ሥጋት የሚሆን ነው፤›› ሲሉ አክለዋል፡፡
‹‹ቁጭ ብለው ተቃውሞ እየገለጹ የሚገኙትን በጉልበት ለመበተን ጥረት አላደረግንም፣ ድንኳኖቹም እዚያው አሉ፣ ወጣቶችም እንደ ልባቸው እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ አብዛኞቹ ተቃዋሚዎች ተቀምጦ መቃወሙን ትተው እየሄዱ ይገኛሉም፤›› ብለዋል፡፡
ሱዳናውያን አል በሽር ከሥልጣን እንዲወርዱ የጀመሩት ተቃውሞ ተሳክቶ አል በሽር ከሥልጣን ቢወገዱም፣ ወታደራዊ መንግሥቱ ሥልጣኑን ለሲቪል በሚያስረክብበት ሁኔታ ላይ ከስምምነት መድረስ አልቻሉም፡፡
የሱዳን ወታደራዊ ካውንስልና ቼንጅ ኤንድ ፍሪደም አሊያንስ ሱዳንን በሽግግር ጊዜ የሚመራ ካውንስል ለመሰየም በተደጋጋሚ በጠረጴዛ ዙሪያ ቢቀመጡም፣ ውጤት አላመጡም፡፡ በመሆኑም ድንኳናቸውን ተክለው አዳራቸውን ውጭ ያደረጉ ባለሙያዎች በየቀኑ ውትወታቸውን ተያይዘውታል፡፡
ሰኞ ዕለት (ግንቦት 26 ቀን 2011 ዓ.ም.) የተከሰተው ግጭትና ሞት አልበሽር ሥልጣን ከለቀቁ በኋላ ያልተለመደ ሲሆን፣ በሱዳን የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲም የሱዳን ፀጥታ ኃይሎች በተቃሚዎች ላይ የወሰዱትን ዕርምጃ ስህተት ብሎ፣ ድርጊቱ እንዲቆም ጥሪ አቅርቧል፡፡