በሰባት ክልሎች በ38 ወረዳዎች በደረሱ የጎርፍ አደጋዎች 42,306 ቤተሰቦች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸውን፣ የብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ በአደጋው ስድስት ሰዎችና 3,256 እንስሳት መሞታቸውን፣ በ6,383.4 ሔክታር ላይ የበቀለ ሰብል መጥፋቱን፣ 62.5 ኩንታል ማዳበሪያ መውደሙን ኮሚሽኑ ለሪፖርተር በላከው ዝርዝር መረጃ ገልጿል፡፡ የጎርፍ አደጋዎቹ የደረሱት ካለፈው ግንቦት ወር ጀምሮ እንደሆነም ታውቋል፡፡
የጎርፍ አደጋው የተመዘገበባቸው 38 ወረዳዎች በደቡብ፣ በአፋር፣ በአማራ፣ በጋምቤላ፣ በኦሮሚያ፣ በሶማሌና በትግራይ ክልሎች እንደሚገኙ የኮሚሽኑ ሪፖርት ያሳያል፡፡
ከግንቦት ወር የጀመረው የጎርፍ አደጋ በአፋር ክልል የሚገኙ 36,000 ቤተሰቦች እንዲፈናቀሉ ምክንያት እንደሆነ ታውቋል፡፡ በአደጋው 2,210 እንስሳት እንደሞቱም ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
ከአፋር ክልል በመቀጠል ከፍተኛ የጎርፍ አደጋ በተመዘገበበት ደቡብ ክልል በ13 ወረዳዎች የጎርፍ ጥቃት ተከስቷል፡፡ በአደጋው 5,958 ቤተሰቦች ከቀዬአቸው እንደተፈናቀሉ፣ በ4,721 ሔክታር ላይ የበቀለ ሰብል እንደወደመ፣ በ150 መኖርያ ቤቶች ላይ ከባድ ጉዳት እንደደረሰ፣ በ13 ትምህርት ቤቶችና በሌሎች የመሠረተ ልማት አውታሮች ላይም መጠነ ሰፊ ጉዳት እንደተከሰተ የኮሚሽኑ ሪፖርት ያሳያል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ 13 ወረዳዎች በደረሰ አደጋም 198 ቤተሰቦች ከቤት ንብረታቸው እንደተፈናቀሉ፣ 80 መኖርያ ቤቶች እንደወደሙ፣ 19 እንስሳት እንደ ሞቱና በ203.4 ሔክታር ላይ የበቀለ ሰብል እንደጠፋ ተመዝግቧል፡፡
መሰል የጎርፍ አደጋዎች በአማራ፣ በጋምቤላ፣ በኦሮሚያ፣ በሶማሌና በትግራይ ክልሎች እንደተመዘገበም ታውቋል፡፡ በመኸር ወቅት የጎርፍ አደጋ ሊያጋጥማቸው የሚችሉ የተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ዝርዝርም በሪፖርቱ ሰፍሯል፡፡
በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የጎርፍ አደጋ እንደሚደርስ መተንበዩ ተገልጿል፡፡ በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋና በሐረርም በተመሳሳይ የጎርፍ አደጋ እንደሚያጋጥም ትንበያው እንደሚያሳይ የኮሚሽኑ ሪፖርት ያመለክታል፡፡