በከፍተኛ የሙስና ወንጀል ተከሰው ከሁለት ዓመታት በላይ በእስር ላይ ሆነው ሲከራከሩ የነበሩት የቀድሞ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣናት ክስ ተቋረጠ፡፡
የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ክስ ያቋረጠላቸው የባለሥልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ፍቃዱ ኃይሌ (ኢንጂነር) እና የተለያዩ ኃላፊነት የነበራቸው ሙሉጌታ አብርሃ (ኢንጂነር)፣ አህመዲን ቡሴር (ኢንጂነር)፣ ዋስይሁን ሽፈራው (ኢንጂነር)፣ እንዲሁም እስራኤላዊው ሚስተር ሜናሼ ሌቪ ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ በግንቦት ወር 2009 ዓ.ም. ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር የዋሉት ከ198.9 ሚሊዮን ብር በላይ በሕዝብና በመንግሥት ላይ ጉዳት አድርሰዋል ተብለው እንደነበር በወቅቱ መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ጉዳቱ ደርሷል የተባለው ባለሥልጣኑ ከትድሃር ኤክስካቬሽን ኤንድ ኧርዝ ሙቪንግ ሊሚትድ ጋር ባደረገው የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክት ውል ጋር በተገናኘ ነበር፡፡ የመንገድ ግንባታው በወቅቱ ከምሥራቅ ወደ ምዕራብ ወይም በተለምዶ ከማዕድን ሚኒስቴር እስከ ውኃ ሀብት ሚኒስቴር የሚደርስ ሲሆን፣ ኃላፊዎቹ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግዥ መመርያ ቁጥር 3/2002 ከሚፈቅደው ውጪ ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ የቅድመ ክፍያና የመልካም ሥራ አፈጻጸም ዋስትና ከኮንትራክተሩ ጋር በመዋዋልና በመፍቀድ 198,872,730 ብር ጉዳት ማድረሳቸው ተገልጾ ነበር፡፡ በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ ክስ መሥርቶባቸው ላለፉት ሁለት ዓመታት ሲከራከሩ የቆዩ ቢሆንም፣ ሰሞኑን ዓቃቤ ሕግ ክሱን ማቋረጡ ታውቋል፡፡
የሪፖርተር ታማኝ ምንጮች ተከሳሾቹ ቀደም ባሉት ጊዜያት የደረሰውን ጉዳት የሚከፍሉ ከሆነ ክሱ እንደሚቋረጥላቸው ሲነገራቸው ባለመስማማታቸው ክርክሩን የቀጠሉ ቢሆንም፣ አሁን ግን ክሱ እንዲቋረጥ መደረጉ ጥያቄ አጭሮባቸዋል፡፡