Friday, June 2, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ለክቡር ሚኒስትሩ የቀድሞ ሚኒስትር ስልክ ደወሉላቸው

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ስብሰባ ላይ ከአንድ ወጣት ጋር ተገናኝተው እያወሩ ነው]

  • ክቡር ሚኒስትር የእውነት ለውጥ አለ፡፡
  • . . .
  • እኔ በእርግጠኝነት መመስከር እችላለሁ፡፡
  • ስለምኑ?
  • ስለለውጡ ነዋ፡፡
  • እንዴት?
  • የዓመታት ጥያቄያችን ሊመለስ እኮ ነው፡፡
  • የምን ጥያቄ?
  • የማንነታችን ጥያቄ ነዋ፡፡
  • የማንነት ጥያቄማ ከተመለሰ ዓመታት ተቆጠሩ እኮ፡፡
  • እኔ የምልዎት የእኛ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡
  • ማለት?
  • ይኸው ክልል ልንሆን እኮ ነው፡፡
  • . . .
  • ለዓመታት ታፍነን ስንኖር ነበር፡፡
  • ምን አልከኝ?
  • ለውጡ እውነተኛ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እናንተ ክልል መሆናችሁ ነው የለውጡ መለኪያ?
  • ምን ጥያቄ አለው?
  • . . .
  • እውነተኛ ዴሞክራሲ መኖሩ ተረጋግጧል፡፡
  • የምን ዴሞክራሲ?
  • በቃ መንግሥት የሕዝቡን ድምፅ መስማት ጀምሯላ፡፡
  • እንዳትሳሳት፡፡
  • ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
  • ለነገሩ አንተ ምኑን ታውቀዋለህ?
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • አሁን አገሪቱ ባለችበት ሁኔታ የክልልነት ጥያቄ ተገቢ ነው?
  • ምን ችግር አለው?
  • ስማ እንኳን ተነጣጥለን ተባብረንም አልቻልነውም እኮ፡፡
  • ምኑን?
  • ችግሩን ነዋ፡፡
  • አንደኛው ችግር እኮ አለመነጣጠላችን ነው፡፡
  • ምን?
  • ይኸው እኛ ክልል ስንሆን የራሳችን በጀት ይኖረናል፡፡
  • ዶሮ ብታልም ጥሬዋን አሉ?
  • ምን ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • በቃ ሁሉም የሚያስበው ከነገሩ እኔ ምን አተርፋለሁ የሚለውን ነው አይደል?
  • እንደዚያ ማሰብ ምን ችግር አለው?
  • ሁሌ እኔ እያሉ ማሰብ እኛን ያስረሳላ፡፡
  • . . .
  • አየህ ሁሉ ከራሱ ጥቅም አንፃር ብቻ ነገሮችን መመልከት ካላቆመ በጋራ መጓዝ አንችልም፡፡
  • ምን ማድረግ ይቻላል?
  • በጋራ ለመጓዝ በጋራ ማሰብ መቻል አለብን፡፡
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
  • አሁን ጊዜው አይደለም እያልኩህ ነው፡፡
  • የምን ጊዜ?
  • የምንነጣጠልበት ጊዜ ነዋ፡፡
  • ምን?
  • አሁን ክልል መሆን አይቻልም፡፡
  • ምን ችግር አለ?
  • እንዴት?
  • መንግሥት ባይፈቅድ እኛ ተሰብስበን እናፀድቀዋለን፡፡
  • በምን?
  • በጭብጨባ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ የክልል ባለሥልጣን ጋር ተገናኝተው እያወሩ ነው]

  • ምን እየሆናችሁ ነው?
  • ምን ሆንን ክቡር ሚኒስትር?
  • ሁሉም ሰው ማሰብ አቆመ ልበል?
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
  • ምነው ትንሽ ሰከን ብትሉ?
  • ምን አደረግን?
  • አሁን አገሪቱ ያለችበትን ሁኔታ አጥታችሁት ነው?
  • አገሪቱ ምን ሆነች?
  • ምን እያልክ ነው?
  • ለውጥ ላይ መሆናችንን ነው የማውቀው፡፡
  • ወይ ይኼ ለውጥ ጉድ አፈላ እኮ?
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • በስመ ለውጥ አገሪቱ ታመሰች እኮ፡፡
  • እኛ እኮ የዓመታት ጥያቄያችን በመመለሱ ነው ለውጥ አለ የምንለው፡፡
  • ኧረ እስኪ ትንሽ ተረጋጉ፡፡
  • የምን መረጋጋት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እስኪ ትንሽ ከራሳችን ባሻገር ስለሌሎችም እናስብ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ተረቱም እኮ ከራስ በላይ ንፋስ አይደል እንዴ የሚለው?
  • ይኼ አካሄድ ማናችንንም አያዋጣንም፡፡
  • ለምን?
  • የጋራ እሴቶቻችን ላይ ብናተኩር ነው ለአንድነታችን የሚያዋጣው፡፡
  • ልዩነታችንም እኮ ጌጥ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እኔ እሱን መቼ ካድኩ?
  • ታዲያ ምን እያሉ ነው?
  • አሁን ጊዜው አይደለም፡፡
  • እንዲያውም ጊዜው አሁን ነው፡፡
  • እንዴት ሆኖ?
  • ለውጥ ላይ ነና፡፡
  • . . .
  • ለውጡ ሳይቀለበስ እኛም ጥያቄያችንን ማስከበር አለብን፡፡
  • ወይ ጣጣ?
  • እርስዎ ግን የእኛ ክልል መሆን ለምን አሳሰበዎት?
  • እናንተ ከጀመራችሁት የሌሎቹም ጥያቄ አያባራማ፡፡
  • ምን ችግር አለው?
  • የእናንተን ከተቀበልን በአገሪቱ ላይ ሌሎች አሥራ አንድ ክልሎች መጨመራችን የማይቀር ነው፡፡
  • ኢኮኖሚያችን ብቻ አይደለም በ11 በመቶ ማደግ ያለበት፣ የክልሎቻችን ቁጥር በ11 መጨመር አለበት፡፡
  • እንግዲህ ሲነገርህ ስማ፡፡
  • ምኑን ነው የነገሩኝ?
  • አሁን ጊዜው አይደለም፡፡
  • ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • አሁን ክልል መሆን አትችሉም፡፡
  • እሱንማ መቀልበስ አይቻልም፡፡
  • ምን?
  • ሕዝቡን ማቆም አይቻልም፡፡
  • ሕዝቡ እኮ እናንተን ነው የሚከተለው፡፡
  • ጥያቄውን እኛም እናምንበታለን እኮ፡፡
  • ሕዝቡን ከኋላ የምትቀሰቅሰው አንተ እንደሆንክ እናውቃለን፡፡
  • ምን ችግር አለው?
  • አርፈህ ተቀመጥ፡፡
  • ባላርፍስ?
  • አንተንም ከልለን እናስቀምጣሃለን፡፡
  • የት?
  • ቂሊንጦ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር ቢሯቸው እያወሩ ነው]

  • ምን ተሻለ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምኑ?
  • የአገሪቱ ጉዳይ ነዋ፡፡
  • እንዴት?
  • በቃ በየጊዜው በችግር ላይ ችግር ነው የሚደረበው፡፡
  • ምን ታደርገዋለህ?
  • ቆም ብሎ የሚያስብ ሰው ጠፋ ማለት ነው?
  • የሚያሳዝንህ እሱ ነው፡፡
  • ፖለቲከኞቻችን እኮ የለየለት ቁማርተኞች ሆነዋል፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ይኸው በሕዝቡ ሕይወት እየቆመሩ ነዋ፡፡
  • . . .
  • ቁማሩ ጠንከር ሲል የባለሥልጣናትንም ሕይወት እየቀጠፈ ነው፡፡
  • ተወኝ እስኪ፡፡
  • በተለይ ሰሞኑን ሁለቱ ወዳጅ ፓርቲዎች ያወጡት መግለጫ ያሳዝናል፡፡
  • . . .
  • ለነገሩ ከወዳጅነት ወደ ባላንጣነት መቀየራቸውን በአደባባይ አሳይተዋል፡፡
  • ሁላችንም ነን ያዘነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በአሁኑ ጊዜ ግን ከእነሱ ይኼ ይጠበቃል?
  • በፍፁም፡፡
  • ቀጥሎ አብረው እንዴት ይሠራሉ?
  • እሱ የሁላችንም የራስ ምታት ነው፡፡
  • እንኳን አጋር ፓርቲ ተቃዋሚዎችም እርስ በርሳቸው እንደዚህ ዓይነት መግለጫ ያወጣሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡
  • ምንም አልተሳሳትክም፡፡
  • ታዲያ አበቃለት ማለት ነው?
  • ማን?
  • ኢሕአዴግ ነዋ፡፡
  • ኧረ የሰይጣን ጆሮ ይደፈን፡፡
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እንዴት እንደዚህ ዓይነት ክፉ ሐሳብ ታስባለህ?
  • ሕዝቡማ ጥሩ ሐሳብ ነው እያለ ነው፡፡
  • ለምን?
  • አገሪቱን ለዚህ ያበቃት ኢሕአዴግ ነው ብሎ ነዋ የሚያስበው፡፡
  • ተው እንጂ፡፡
  • እውነቴን እኮ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ኢሕአዴግ ከፈረሰ አገሪቱም እንደምትፈርስ አታውቅም?
  • ክቡር ሚኒስትር ኢትዮጵያ እኮ ከኢሕአዴግ በፊት ነበረች፡፡
  • . . .
  • ስለዚህ እያሰቡ እንዲያውም ጥሩ ዕድል ሊሆን ይችላለ፡፡
  • የምን ዕድል?
  • ለእውነተኛው የአገሪቱ ለውጥ ነዋ፡፡
  • ተው ስልህ፡፡
  • እኔ እንዲያውም ማሠራት ልጀምር ነው፡፡
  • ምንድነው የምታሠራው?
  • የአበባ ጉንጉን ነዋ፡፡
  • የምን የአበባ ጉንጉን?
  • መቃብር ላይ የሚቀመጥ፡፡
  • የማን መቃብር ላይ?
  • የኢሕአዴግ!

[ለክቡር ሚኒስትሩ የቀድሞ ሚኒስትር ስልክ ደወሉላቸው]

  • አሁንስ መላ ቅጡ ጠፋችሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን?
  • ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር ሲይዙት ያደናግር አሉ፡፡
  • ምን ለማለት ነው?
  • እንዲያው ሥልጣኑን እኛ ላይ ስታዩት ቀላል መስሏችሁ ነው አይደል?
  • ምን የተለየ ነገር ሠራችሁና?
  • ይኸው እናንተ እኮ ቅጥ አምባሩ ጠፍቶባችኋል፡፡
  • እንዴት?
  • ሕወሓትና አዴፓ የቃላት ጦርነት ጀምረዋል፡፡
  • እሱ የዴሞክራሲ መገለጫ ነው፡፡
  • እየተዋወቅን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ማለት?
  • ይኸው ትግራይ ክልል አኩርፎ ከማዕከላዊ መንግሥት ከተነጣጠለ ሰነባበተ፡፡
  • ኩርፊያው ሲለቃቸው ይመለሳሉ፡፡
  • አማራ ክልል ያለውን ትርምስ መቼም ለእርስዎ አልነግርዎትም?
  • እንደዚህ ዓይነት ፈተና ያጠነክረናል፡፡
  • ይኸው ደቡብ ክልል ተበታትኖ በመንደር መደራጀት ተጀምሯል፡፡
  • እሱም ቢሆን የዓመታት ጥያቄ ነው፡፡
  • ኦሮሚያም ቢሆን ከኦነግ የገጠመው ፈተና ያልተጠናቀቀ ነው፡፡
  • ስለእሱ አታስብ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ሌሎቹም የአገሪቱ ክልሎችም ቢሆኑ የግጭቶች መናኸሪያ መሆናቸው ግልጽ ነው፡፡
  • የእናተው ሥራ ነዋ፡፡
  • ይልቁንስ ጣት መጠቆሙን ትታችሁ ሥራችሁን በአግባቡ ሥሩ፡፡
  • የምን ሥራ?
  • የፌዴራል መንግሥቱ እኮ ክፉኛ ተዳክሟል፡፡
  • ማን ነው ያለው?
  • እየነገርኩዎት አሁን እኮ የፌዴራል መንግሥቱ በአግባቡ እያስተዳደረው ያለው አዲስ አበባን ብቻ ነው፡፡
  • ምን?
  • እንዲያውም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምን እንደተባሉ አልሰሙም?
  • ምን ተባሉ?
  • አዲስ አበባን በምክትል ከንቲባነት የሚያስተዷድሯት አውቀው ነው፡፡
  • ማለት?
  • እሳቸው የከተማዋ ምን እንደሚባሉ ያውቃሉ?
  • ምን ይባላሉ?
  • ቀዳማይ ከንቲባ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

ብሔራዊ ባንክ ለጥቃቅንና አነስተኛ ብድሮች ዋስትና መስጠት ሊጀምር ነው

ኢንተርፕራይዞችን ብቻ የሚያገለግል የፋይናንስ ማዕከል ሥራ ጀመረ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ...

አዋሽ ባንክ ለሁሉም ኅብረተሰብ የብድር አገልግሎት የሚያስገኙ ሁለት ክሬዲት ካርዶች ይፋ አደረገ

አዋሽ ባንክ ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች በዘመናዊ መንገድ ብድር ማስገኘት...

መንበሩ ካለመወረሱ በስተቀር መፈንቅለ ሲኖዶስ መደረጉን ቤተ ክህነት አስታወቀ

ቅዱስ ሲኖዶስ ከነገ ጀምሮ ውይይት እንደሚጀምር ተነገረ ‹‹እኛ ወታደርም ሆነ...

የተጨማሪ እሴት ታክስ አዋጅን የሚተካ ረቂቅ ተዘጋጀ

ከቫት ነፃ የነበረው የኤሌክትሪክ ኃይል ገደብ ተቀመጠለት የገንዘብ ሚኒስቴር ከሃያ...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...

የባንኮች ብድር አሰጣጥ ፍትሐዊና ብዙኃኑን ያማከለ እንዲሆን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አሳሰበ

ባንኮች የብድር አገልግሎታቸውን በተቻለ መጠን ፍትሐዊ፣ የብዙኃኑን ተጠቃሚነት ያማከለና...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ አምሽተው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ‹‹ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ሕዝባችንን እናሻግራለን›› የሚለውን የቴሌቪዥን ዜና ተመልክተው ለብቻቸው ሲስቁ አገኟቸው]

ስልክ እያወራሽ ነበር እንዴ? ኧረ በጭራሽ... ምነው? ታዲያ ምንድነው ብቻሽን የሚያስቅሽ? አይ... በቴሌቪዥኑ የሚቀርበው ነገር ነዋ። ምንድነው? ድሮ ድሮ ዜና ለመስማት ነበር ቴሌቪዥን የምንከፍተው፡፡ አሁንስ? አሁንማ ቀልዱን ተያይዘውታል... አንተ ግን በደህናህ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...

[ክቡር ሚኒስትሩ አየር መንገዱ ወጪ ቆጣቢ የሥራ እንቅስቃሴ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ግኝቱን በሚያሳድግበት ሁኔታ ላይ ከተቋሙ ኃላፊ ጋር እየተወያዩ ነው]

ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ትልቁ ወጪያችን ለነዳጅ ግዥ የሚውለው ነው። ክቡርነትዎ እንደሚገነዘቡት የዩክሬን ጦርነት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በእጅጉ አሻቅቧል። ቢሆንም አገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ችግር ውስጥ...