በደቡብ ክልል እየተነሱ ያሉ በክልል ራስን የማደራጀት ጥያቄዎችን ‹‹በሳይንሳዊ መንገድ ለማጥናት›› በሚል በደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢሕዴን) 10ኛ ጉባዔ ውሳኔ መሠረት የተቋቋመው የአጥኚዎች ቡድን በክልሉ እየተነሱ ያሉ ጥያቄዎችን ከጥቅምና ጉዳቱ አንፃር መዝኖ መልስ ለመስጠት ያስችላሉ ያላቸውን ሦስት ምክረ ሐሳቦችን አቀረበ፡፡
ክልሉ በአሁኑ ቅርፅ መቋቋሙ ያስገኘውን ትሩፋትና ጉዳቶች እንደመዘነ የገለጸው 20 አባላት ያሉት የአጥኚዎች ቡድን፣ በርካታ ጥቅሞችና ያነሰ ጉዳት ያለው አደረጃጀት ክልሉን በአሁኑ ቅርፅ ማስቀጠል የመጀመሪያው ምክረ ሐሳብ እንደሆነ በማስታወቅ፣ ይኼም በክልሉ አብሮነት የተገኙ ትሩፋቶችን ለማስቀጠል ያስችላል ብለዋል፡፡
ለዚህ መነሻም በክልሉ እየታዩ ያሉ ኢፍትሐዊነቶችን ለመፍታት መረጃ የተሰበሰበባቸው ዞኖች ነዋሪዎች የራስን ክልል መመሥረት በሚለው እንደማያምኑበት ያስታወቁ ሲሆን፣ ከሲዳማ ዞንና ከሐዋሳ ከተማዎች ውጪ በሁሉም ክልሎች የተሰበሰበው 17,600 መረጃ ይኼንን ያሳያል ብለዋል፡፡
ይኼ የሚሆን ከሆነም፣ ክልሉ አሁን እንዳለው በአንድ ማዕከል ብቻ የተዋቀረ ሳይሆን በርካታ ማዕከላት እንዲኖሩት ሐሳብ ያቀረበ ሲሆን፣ የክልሉ ቢሮዎችን በመበተን ወይንም በሌላ መንገድ ይኼንን ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል ሲሉም መክረዋል፡፡
ሆኖም ምክረ ሐሳቡን ለመተግበር በከፍተኛ ስሜት የታጀበውና በምክር ቤት ከጸደቀው ጥያቄ ወደኋላ ለመመለስና ክልልነትን ያጸደቁት የየዞኑ ምክር ቤቶች ሕዝቡን በዚህ ሐሳብ ለማሳመን ያዳግታቸዋል ሲሉ ሥጋታቸውን የገለጹ ሲሆን፣ ክልሉ እንዳለ ቢቀጥልና አሁን እየታዩ ያሉ ችግሮችን መፍታት ካልታቻለ ግን ካሁኑ የባሰ ችግር ሊከሰት ይችላል ሲሉም አስጠንቅቀዋል፡፡
ሁለተኛው ምክረ ሐሳብ ክልሉን በሁለት ወይንም ከዛ በላይ በሆኑና በደረጃ ብዙሃኑን የሚያቅፉ ክልሎችን ማቋቋም ሲሆን፣ ይኼ አንፃራዊ የኢኮኖሚ ፋይዳዎችን ይዞ ሊመጣ እንደሚችል አጥኚዎቹ አስረድተዋል፡፡ ክልሉ የዕምቅ ሀብት ባለቤት ሆኖ ሳለ በአንድ ማዕከል መታጠሩን በመጠቆም፣ የተለያዩ ክልሎችን በማቋቋም የየራሳችንን ማዕከል እናልማ የሚል ጥያቄ እንዳለና ለዚህ ምላሽ መስጠት እንደሚቻልም ገልጸዋል፡፡
ይኼ ሁሉ የማይሆን ከሆነ ግን አሁን ያለው ስሜታዊነት እንዲረግብና ለባሰ አገራዊ ደኅንነት ሥጋት ምንጭ እንዳይሆን የክልልነት ጥያቄዎችን ለጊዜው ማቆየት ይበጃል የሚለውን በሦስተኛ ምክረ ሐሳብነት ቀርቧል፡፡
የጥናቱ ውጤት ለደኢሕዴን ቀርቦ በማዕከላዊ ኮሚቴ ውይይት እንደተረገበት የተገለጸ ሲሆን፣ የጥናቱን ግኝትና ምክረ ሐሳቦችን በሚመለከት በክልሉ በሁሉም ዞኖች በሚገኙ ወረዳዎች ውይይቶች እንደሚካሄዱም ተገልጿል፡፡