የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያሳዩት በኢትዮጵያ በስፋት ከሚታዩ በሽታዎች አንዱ የማሕጸን በር ካንሰር ነው፡፡ የማሕጸን ጫፍ ካንሰር ከጡት ካንሰር ቀጥሎ በብዛት ተሰራጭቶ የሚገኝ በሽታ ነው፡፡ በሽታው ሲጀምር የሚታዩ ምልክቶች ባይኖሩም፣ በቅድመ ምርመራ መኖሩ ከተረጋገጠ ውጤታማ ፈውስ የሚገኝበት ሕክምና መኖሩንም ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
በኢትዮጵያ የማሕጸን በር ካንሰር ሥርጭቱ ከፍተኛ ከመሆኑ አንፃር ከዘጠኝ ሚሊዮን በላይ የሆኑ ዕድሜያቸው ከ30 እስከ 49 የሚሆኑ ሴቶች የማሕጸን በር ካንሰር ቅድመ ልየታ እንደሚያስፈልጋቸው ከዚህ ቀደም ተነግሯል፡፡
ሳንቴ የሕክምና ኮሌጅ “Common Cancers in Ethiopia with Emphasis on Prevention and Management of Cervical Cancer” በሚል መሪ ቃል አራተኛውን የምርምርና ጥናት ጉባኤና የጤና ኤግዚቢሽን ቅዳሜ ሐምሌ 20 ቀን 2011 ዓ.ም. አካሂዷል፡፡
አራተኛው የምርምርና ጥናት ጉባኤ ለካንሰር በተለይም ለማሕጸን ጫፍ ካንሰር ልዩ ትኩረት የሰጠ ሲሆን፣ በካንሰርና በማሕጸን በር ካንሰር ዙሪያ የተዘጋጁ ጥናታዊ ጽሑፎችም ቀርበዋል፡፡ የሕክምና ባለሙያዎችም በሽታውን ለመከላከልና ባለበት ለማቆም ስለሚቻልበት ሁኔታ ልምድና ተሞክሯቸውን አቅርበዋል፡፡
ጤና ሚኒስቴርን የወከሉት ወ/ሮ ታከለች ሞገስ፣ የካንሰር መከላከልና መቆጣጠር ትኩረት ሳያገኝ የቆየ የጤና ዘርፍ እንደሆነ በመግለጽ፣ ላለፉት አምስት ዓመታት በፖሊሲና ስትራቴጂ ደረጃ የተሰጠው ትኩረት የሚያበረታታ ነው ብለዋል፡፡
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር የድርጊት መርሐ ግብር መኖሩ፣ የካንሰር መከላከልና መቆጣጠር የአምስት ዓመት ዕቅድ መዘጋጀቱ እንዲሁም የማሕጸን በር ካንሰር ቅድመ ልየታና ሕክምና በስፋት እንዲሠራ ዕቅድ ተነድፎ ወደ ተግባር መገባቱንም ለአብነት አንስተዋል፡፡
በቅርቡ የዓለም ጤና ድርጅት ያወጣው የማሕጸን በር ካንሰርን ከዓለም የማጥፋት ዕቅድ ከማሕጸን በር ካንሰር ጋር በቀጥታ እንደሚገናኝ በመግለጽም፣ ኢትዮጵያም የዚሁ ዕቅድ አካል ለመሆን እየሠራች ነው ብለዋል፡፡
90 በመቶ ለሚሆኑ ዕድሜያቸው ከዘጠኝ እስከ 14 ዓመት የሆኑ ታዳጊ ልጃገረዶችን ክትባት የመስጠት 70 በመቶ በተለይም ዕድሜያቸው ከ35 እስከ 45 ያሉ ሴቶችን የቅድመ ካንሰር ምርመራዎችን ማድረግና ዘጠና በመቶ በካንሰር የተያዙ ሴቶችን ማግኘትና ወደ ሕክምና ለመውሰድ የሚያስችል ስትራቴጂ እንደተነደፈም ተናግረዋል፡፡
በማሕጸን በር ካንሰር ቅድመ ልየታና ሕክምናዎችን ለማስፋፋት አንድ ሺሕ አምስት መቶ ክራዩማሽኖች ግዥ በሚኒስቴሩ በማከናወን በእያንዳንዱ ወረዳዎች ጤና ተቋማት ተመርጠው አገልግሎት እንዲጀምሩ ለባለሙያዎች ሥልጠና በመስጠት ላይ እንደሚገኙ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ለሆኑ ታዳጊ ልጃገረዶች (ዕድሜያቸው 14 ዓመት የሆኑ) የማሕጸን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት ተጠቃሚ መደረጋቸውን፣ አምስት የካንሰር ማዕከላትን ለመገንባት በሒደት ላይ እንዳሉ እንዲሁም የሃሮማያ ሕይወት ፋና ሆስፒታልና የጂማ ዩኒቨርሲቲ ሆስፒታል ግንባታ ተጠናቆ የመሣሪያ ተከላው ተከናውኖ ሥራ ለመጀመር ዝግጅት ላይ እንደሆኑ አስታውቀዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሣይንስ ኮሌጅ የካንሰር ሕክምና ስፔሻሊስት ማቴዎስ አሰፋ (ዶ/ር)፣ የማሕጸን በር ጫፍ ካንሰር በቫይረስ የሚመጣ የካንሰር ዓይነት ነው ይላሉ፡፡ ይህ ቫይረስ (Human Papilloma Virus) ወይም ኤችፒቪ የሚባል ሲሆን፣ የማሕጸን ጫፍ ላይ ኢንፌክሽን ፈጥሮ ለረዥም ጊዜ ከቆየ በኋላ ጤነኛ ሴሎችን ወደ ካንሰር ሴልነት በጊዜ ሒደት ይቀይራቸዋል፡፡ ሒደቱ ረዥም ጊዜ የሚፈጅ ሲሆን፣ በአብዛኛው የሚፈጠረውም በልቅ ግብረ ሥጋ ግንኙነት ጊዜ ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ሴቶች በዚህ በሽታ ተጠቂ የሚሆኑት ግብረ ሥጋ ግንኙነት ከጀመሩ በኋላ መሆኑን፣ ነገር ግን ኢንፌክሽኑ ከተከሰተ በኋላ ወደ ካንሰር እስኪለወጥ እስከ 20 ዓመት የሚፈጅበት ጊዜም እንዳለና፣ ወደካንሰር ሳይለወጥ ቀድሞ መታከም እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡
በዚህ ጊዜ ውስጥ የሚከሰቱ የተለያዩ የቅድመ ካንሰር ለውጦች እንዳሉ የገለጹት ዶ/ር ማቴዎስ፣ ኢንፌክሽኑ ከተከሰተባቸው ሴቶች መካከል አብዛኛዎቹ ከ80 እስከ 90 በመቶ የሚሆኑት ካንሰሩን ሰውነታቸው መከላከያ በማበጀት ቫይረሱን መሉ በሙሉ ያስወግደዋል፣ የተወሰኑት ደግሞ ወደ 15 በመቶ የሚሆኑት ሰውነታቸው ቫይረሱን ማስወገድ ሳይችል ይቀርና ቫይረሱ ለረዥም ጊዜ በማሕጸን ጫፍ ላይ በመቆየት ጤነኛ የሆኑትን ሴሎች ይቀይራቸዋል ብለዋል፡፡
የማሕጸን ጫፍ ካንሰር ሙሉ በሙሉ መከላከልም ማስወገድም የሚቻልበት ደረጃ ላይ እንደተደረሰ የሚናገሩት ዶ/ር ማቴዎስ፣ አንዲት ሴት የቅድመ ካንሰር ምርመራ ብታደርግ ካንሰር ከመከሰቱ በፊት የቅድመ ካንሰር ደረጃውን አውቃ ሕክምና ተደርጎ ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠርና ማዳን ይቻላል ሲሉም አስረድተዋል፡፡
የማሕጸን በር ካንሰር አምጪ ቫይረሶች ከ200 ዓይነት በላይ ሲሆኑ፣ በአብዛኛው ለዚህ ካንሰር የሚያጋልጡት ቁጥር 16 እና ቁጥር 18 የሚባሉት ናቸው፡፡ ቁጥር 6 እና ቁጥር 11 የሚባሉት ቫይረሶች ደግሞ ማሕጸን አካባቢ የማሕጸን ኪንታሮት የሚባለውን የሚያመጡ እንደሆነ፣ ለዚህ የሚሰጠው ክትባትም ሴቶች ግብረ ሥጋ ግንኙነት ከመጀመራቸው በፊት መሆኑንና ይህ ክትባት አንዴ ከተሰጠ በኋላ በአንድ ወር ወይም በሁለት ወር ከዚያም ከስድስት ወር በኋላ በመድገም እንደሚቻል አክለዋል፡፡ ሙሉ በሙሉ ኢንፌክሽኑም ካንሰሩንም መከላከል ይቻላል፤›› ብለዋል፡፡
ከኤችአይቪ ጋር ስላለው ግንኙነት ሲገልጹም፣ ‹‹ማንኛውም ቫይረስ ኤች አይቪ በሚኖርበት ጊዜ ደረጃውም የመሰራጨት አቅሙም ከፍተኛ እንደሚሆን፣ የሰውነት በኤች አይቪ የተያዙ ሴቶች የመከላከያ አቅማቸው ስለሚዳከም ወደ ካንሰርነትና ቅድመ ካንሰር የመቀየር ሁኔታውን እንደሚጨምር ተናግረዋል፡፡
ክትባቱን የጤና ሚኒስቴር እያስተባበረው ባሉት ጤና ድርጅቶች በአገሪቱ በሙሉ የሚሰጥ ሲሆን፣ ሕክምናውም ደግሞ በቀዶ ሕክምና፣ በጨረርና በኬሞቴራፒ መልክ እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡
የጨረር ሕክምና በጥቁር አንበሳ ብቻ የሚሰጥ ሲሆን፣ የቀዶ ሕክምናው በጥቁር አንበሳ፣ በቅዱስ ጳውሎስና በሌሎች የክልል ሆስፒታሎች እንደሚሰጥም አክለዋል፡፡
ከ100,000 ሴቶች 24ቱ የማሕጸን በር ካንሰር እንደሚይዛቸውና በየዓመቱ 8,000 ሴቶች በዚህ በሽታ እንደሚጠቁ የዓለም ጤና ድርጅት በቅርቡ ይፋ ያደረገው መረጃ ያትታል፡፡
እ.ኤ.አ. በ2018 በማሕጸን በር ካንሰር 311,000 ሴቶች መሞታቸውን፣ ከዚህም ውስጥ ከ85 በመቶ በላይ የሚሆኑት የሚገኙት መካከለኛና አነስተኛ ገቢ ባላቸው አገሮች ውስጥ መሆኑን መረጃው አክሏል፡፡