Thursday, June 1, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ኪንና ባህልየቡሔ ወግ በያጥናፉ

የቡሔ ወግ በያጥናፉ

ቀን:

‹‹ነሐሴ የተስፋ ምልክት፣ የምሥራች ዋዜማ፣ የብርሃን ተምሳሌት ናት፡፡ እሸት አዝላ፣ አበባ ታቅፋ፣ ብቅ ስለምትል ለገበሬው የተስፋ ምልክቱ ናት፡፡ ነሐሴ ደግሞ በቡሔዋ ትለያለች›› ይሉናል መምህራኑ፡፡ ነሐሴ ወደ አጋማሿ ዋዜማ ላይ ብቅ የሚለው የቡሔ በዓል አከባበር በመጠኑም ቢሆን ከቦታ ቦታ ይለያያል፡፡ በዓሉ በተለያዩ አካባቢዎች ከዋዜማው ነሐሴ 12 ቀን ጀምሮ የሚከበረው ምሽቱ ላይ ችቦ የሚለኮሰው የነሐሴ 12 ማታ በሥርዓተ አምልኮ ቀን (ሊተርጂካል ዴይ) አቆጣጠር የነሐሴ 13 መነሻ ነውና፡፡

የቡሔ ወግ በያጥናፉ

ቡሔ ምን ማለት ነው?

እንደ መዛግብተ ቃላቱ፣ ቡሔ ማለት ብርሃን፣ ገላጣ ወይም የብርሃን መገለጥ፣ የብርሃን መታየት፣ መጉላት ብሩህ መሆን ማለት ነው፡፡ ቡሔ የበዓል ስምም ነው፡፡ ስሙም ከግብሩ ተገኝቷል፡፡ በደብረ ታቦር ቧ ብሎ የተገለጸውን የጌታችንን የፊቱን ብርሃን ጸዳል ያስረዳል፡፡

ደብረ ታቦር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ሦስት ደቀመዛሙርቱን ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ እሑድ ነሐሴ 13 ቀን 33 ዓ.ም. ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደ ፀሐይ  የበራበት ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ የሆነበት ቦታ ነው፡፡ በማቴዎስ ወንጌል  እንደተጻፈው ኢየሱስ  ከሙሴና ኤልያስ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። 

በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ደብረ ታቦር ተብሎ የሚታወቀው ዓመታዊ በዓል በአውሮፓ ቋንቋዎች ‹‹ትራንስፊጉሬሽን›› (Transfiguration) ይባላል፡፡ በኢትዮጵያ ነሐሴ 13 ቀን፣ በአውሮፓዎች ኦገስት 6 ቀን ሲከበር ከወቅት አንፃር የኢትዮጵያው በክረምት አጋማሽ የአውሮፓው በበጋ አጋማሽ  ይውላል፡፡

ድርሳናት እንደሚያሳዩት የቡሔ በዓል መጀመርያ የተከበረው በአራተኛው ምዕት ዓመት በሶሪያ ሲሆን፣ በምዕራብ ቤተ ክርስቲያን መከበር የጀመረው በአሥረኛው ምዕት ዓመት በፈረንሳይ ነው፡፡ የሚውልበትም ኦገስት 6 (ነሐሴ 13) በደብረ ታቦር ላይ የመጀመርያው ቤተክርስቲያን የተተከለበት ዕለት ናት፡፡ የመለኮቱ ብርሃን የተገለጠበት ‹‹ከፍተኛ ተራራ›› ተብሎ የሚታሰብበት ቦታ ነው፡፡

በምዕራብ ቤተ ክርስቲያን መከበር የጀመረው በአሥረኛው ምዕት ዓመት በፈረንሳይ ነው፡፡ እስከ 1457 ዓመተ እግዚእ ድረስም ከምዕራብ ክርስቲያን የበዓላት ዝርዝር አልገባም ይለናል episcopalchurch የተባለው ገጽ፡፡ 

በኢትዮጵያ መቼ ማክበር ተጀመረ?

በአንደኛው ምዕት በቅዱስ ባኮስ በሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ ክርስትና የተሰበከባት ኢትዮጵያ ከአራተኛው ምዕት ጀምሮ በመጀመርያው ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ፍሬምናጦስ በይቀጥላልም በተሰዓቱ ቅዱሳን የበዓላት ትውፊቱም ሥርዓቱም እንደቀጠለ ይታመናል፡፡ በስድስተኛው ምዕት የቅዱስ ያሬድ ድጓ የደብረ ታቦር በዓል (ነሐሴ 13) መዝሙር ሠርቶለታል፡፡ በዓሉ በአገራችን ከዘመነ አክሱም ጀምሮ እየተከበረ ያለ በዓል ነው፡፡

የክረምቱ ቡሔ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዓሉ በዋናነት ደብረ ታቦር መባሉ እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ ክብሩን የገለጠበት ሥፍራ ደብረ ታቦር በመሆኑ ነው፡፡ መምህራን እንደሚገልጹት ቡሔ የሚለውም ብርሃንን ይጠቅሳል፡፡

 በኢትዮጵያ ቡሔ የሚከበረው በክረምት ወቅት ነው፡፡ ክረምት እንደሚታወቀው ከሰኔ 26 ቀን እስከ መስከረም 25 ቀን ድረስ ባሉት 95 ቀናት ውስጥ ይዘልቃል፡፡ የቡሔው ዕለት የሚውልበት ነሐሴ 13 ቀን ደግሞ የክረምት አጋማሽ ነው፡፡ (ዘንድሮ ቡሔ ነሐሴ 13 ቀን 2011 .. በጁሊያን አቆጣጠር ኦገስት 6 ቀን 2019 ሲሆን፣ በግሪጎሪያን ቀመር ኦገስት 19 ቀን 2019 ይሆናል)፡፡

ምሥራቆቹ ኦርቶዶክሳውያን በሚከተሉት የጁሊያን አቆጣጠር መሠረት ‹‹ኦገስት 6›› የሚውለው (የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አንዷ ነች) በኢትዮጵያ ነሐሴ 13 ቀን ላይ ነው፡፡ ምዕራቦቹና ከምሥራቅ የተወሰኑት በሚከተሉት የግሪጎርያን አቆጣጠር መሠረት ‹‹ኦገስት 6›› የሚውለው ሐምሌ 30 ቀን (በጁሊያን ጁላይ 24 ቀን) ነው፡፡

የበጋው ቡሔ

ካርዲናል ቲሞቲ ዶላን እንደሚገልጹት በበጋማው የኦገስት ወር በቤተ ክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ የደስታ ብርሃን የሚንፀባረቅባቸው የበዓላት ቀኖች ቡሔና ፍልሰታ ናቸው፡፡ አንደኛው ቡሔ ኦገስት 6 የሚውልበት ቀን የበጋ ወቅት አጋማሽ (ሚድ ሰመር) ላይ የሚውልበት ልዩ አጋጣሚ ነው፡፡ እንደሚታወቀው በአውሮፓው ባሕረ ሐሳብ መሠረት በጋ (ሰመር) የሚቆየው ከጁን 21 ቀን እስከ ሴብቴምበር 23 ቀን ድረስ ሲሆን፣ አጋማሹም ኦገስት 6 ላይ ይሆናል፡፡ በዚህ የበጋ አጋማሽ ላይ ነው እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ ታቦር ተራራ ላይ ከሐዋርያት ጋር ከወጣ በኋላ መለኮታዊ ብርሃኑ የተገለጠው፣ ‹‹የምወደው ልጄ ይህ ነውና እሱን ስሙት›› የተሰማው፡፡

አውሮፓውያኑ ለበጋው አጋማሽ ልዩ ሥፍራ ይሰጡታል፡፡ ዕረፍት የሚወጡበት፣ ቤተሰብና ጓደኛን የሚጎበኙበት የደስታና የመዝናናት ጊዜን ያሳልፉበታል፡፡

ቡሔ ከሚከበርባቸው አገሮች አንዷ ስለሆነችው ቡልጋሪያ አልቤና ቤዞቭስካ እንደጻፉት፣ የቡሔ ዕለት ማለዳ ላይ ምዕመናን ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚያቀኑት በወቅቱ የደረሰ የወይን ዘለላን ይዘው ነው (በጃፓን ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንም በቡሔ ዕለት የደረሰውን ፍራፍሬ ይዘው ይቀርባሉ)፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ቡራኬ ከተሰጠ በኋላ ሴቶች ወይኑን ለቤተሰቦቻቸውና ለጎረቤቶቻቸው ያድላሉ፡፡ እነሱም ያጣጥሙታል፡፡ በሌሎች የአገሪቱ ከተሞች የተለያዩ ፍራፍሬዎች እንደ አፕል፣ ሃብሃብ (ወተር ሜለን) ያሉትም ከቤተ ክርስቲያን ይዘልቃሉ፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...