ከሦስት ዓመት በፊት ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. በፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የቂሊንጦ እስረኛ ማቆያን አቃጥለዋል ተብለው ተከሰው የነበሩና ነሐሴ 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጥፋተኛ የተባሉ አራት ተከሳሾች፣ የፈጸሙት ጥፋት እንደሌለ በመናገር የቅጣት ማቅለያ እንደሚያቀርቡ ለፍርድ ቤት አስታወቁ፡፡
ተከሳሾቹ ክሱን እያየው ለሚገኘው ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት ሰኞ ነሐሴ 13 ቀን 2011 ዓ.ም. እንደገለጹት፣ ከቂሊንጦ እስረኛ ማቆያ ቃጠሎ ጋር በተያያዘ ሊጠየቁ የሚገባቸው አካላት እያሉ እነሱ ሊጠየቁ አይገባም፡፡
ከማረሚያ ቤቱ ቃጠሎ ጋር በተያያዘ በወቅቱ በማረሚያ ቤቱ የተለያዩ ኃላፊነቶች የነበራቸው ሰዎች ክስ ተመሥርቶባቸው እንደሚገኙ ጠቁመው፣ ተፈጽሟል የተባለው ወንጀልም እነሱን እንደማይመለከት አስረድተዋል፡፡
ተከሳሾቹ አቶ ጌታቸው እሸቴ፣ አቶ ፍፁም ጌታቸው፣ አቶ ቶፊክ ሽኩርና አቶ ሸምሱ ሰይድ ናቸው፡፡ ነሐሴ 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተብለው የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርቡ የተቀጠሩ ቢሆንም፣ ‹‹ባልፈጸምነው የወንጀል ድርጊት የቅጣት ማቅለያ አናቀርብም፤›› ብለዋል፡፡
ቃጠሎ በተፈጸመበት ወቅት የግንቦት ሰባት አባላትን ጨምሮ ከ159 በላይ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው እንደነበር አስታውሰው፣ ሁሉም ሲለቀቁ እነሱ ብቻ መቅረታቸውንም ተናግረዋል፡፡ እነሱም በጉዳዩ እጃቸው እንደሌለበትና ነፃ መሆናቸውንም ደጋግመው አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ያላቸው በዓቃቤ ሕግ የቀረበለትን ክስ፣ የሰውና የሰነድ ማስረጃ ከሕጉ ጋር በመመርመርና በማገናዘብ መሆኑን ጠቁሞ፣ ተከሳሾቹ በተከላካይ ጠበቃቸው አማይነት በጽሕፈት ቤት በኩል ማቅለያ ማቅረብ ከፈለጉ የሚችሉ መሆኑን በመንገር፣ ቅጣት ለመወሰን ለጥቅምት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡