የቻይና መንግሥት 250 ሚሊዮን ብር ወጪ በማውጣት ለ228 ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድል ማመቻቸቱን አስታወቀ፡፡
በተመቻቸው ነፃ የትምህርት ዕድል ሐሙስ ነሐሴ 30 ቀን 2011 ዓ.ም. በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ለተማሪዎቹ የሽኝት ፕሮግራም የተደረገ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በሽኝቱ ወቅት ተገኝተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በበርካታ አስከፊ ሁኔታዎች ውስጥ ያለፈችውን አፍሪካና ኢትዮጵያ ነፃ ማውጣት የሚችለውና ጨለማውን የሚያበራው ዕውቀት ብቻ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ችግር የሚፈታው ማሰብ፣ ማሰላሰል፣ መፈላሰፍ፣ እንዲሁም ነገን ማየት የሚችሉ ሰዎች ሲበራከቱ ብቻ ነው፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ቻይና አታስፈልገንም ብንል ኖሮ 228 ሰዎች ቻይና ባልሄዱ ነበር፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹እናንተ ቻይና ውስጥ ኢትዮጵያውያን ናችሁ፡፡ ዘራችሁ፣ ማንነታችሁ ኢትዮጵያዊነት ነው፤›› ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የቻይናንን የኋላ ታሪክ በማስታወስ፣ ቻይና ዓለም በፈጠነበት ጊዜ ወደ ኋላ መቅረትን በተግባር እንዳየች አስረድተዋል፡፡ አሁን ደግሞ፣ ‹‹ከቻይናውያን መማር ያለባችሁ እናደርገዋለን የሚል ወኔን ነው፤›› ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የቻይና መንግሥት ግለሰቦችን ለማስተማር የሚያደርገውን ድጋፍ በማመሥገን፣ ተማሪዎቹም በሁለቱ አገሮች መካከል እንደ ድልድይ ሆነው እንደሚያገለግሉ አስረድተዋል፡፡
ቻይና በሰጠችው የነፃ የትምህርት ዕድል ከሁሉም የፌዴራል ሚኒስትር መሥሪያ ቤቶችና የክልል መንግሥታት የተውጣጡ ባለሙያዎች ተጠቃሚ መሆናቸው ታውቋል፡፡
ይህ ዕድል 90 አገሮችን ተጠቃሚ የሚያደርግ እንደሆነ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ 1,380 ተማሪዎችንም ተሳታፊ ያደርጋል በማለት ቀዳሚ ተጠቃሚዋ ኢትዮጵያ እንደሆነች ተናግረዋል፡፡
ነፃ የትምህርት ዕድሉ የተሰጠው በሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ለመሠልጠን በተመረጡ ተማሪዎች ናቸው፡፡ 66 ተማሪዎች በፒኤችዲ መርሐ ግብር፣ እንዲሁም 162 ተማሪዎች በማስተርስ መርሐ ግብር ተሳታፊ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡
ቻይና እ.ኤ.አ በ2018 ከሰባት ሺሕ በላይ ለሚሆኑ ባለሙያዎች የአጭር ጊዜ ሥልጠና፣ እንዲሁም ለ300 ደግሞ ነፃ የትምህርት ዕድል እንደሰጠች ተጠቁሟል፡፡
በኢትዮጵያ የቻይና ኤምባሲ የኢኮኖሚና የንግድ ካውንስለር እንደገለጹት፣ ተማሪዎቹ የተመቻቸላቸው የትምህርት ዕድል እንደ ፍላጎታቸው አንድ ዓመት ወይም ሁለት ዓመት የሚቆይ ነው፡፡
ከነፃ የትምህርት ዕድሉ በተጨማሪ ለ800 ሰዎች የአንድ ወር አጭር ሥልጠና እንደሚሰጥም አክለዋል፡፡