በኦሮሚያ ክልል በምዕራብና በደቡብ ዞኖች አካባቢዎች እስካሁን ታጣቂዎች እንዳሉና እየተንቀሳቀሱ ጥቃት እንደሚፈጽሙ፣ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ፡፡ ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ይኼንን ያሉት ቅዳሜ ጳጉሜን 2 ቀን 2011 ዓ.ም. በጽሕፈት ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፡፡
በ2011 ዓ.ም. የዴሞክራሲ ምኅዳሩን ለማስፋትና አዲስ የፖለቲካ ባህል እንዲመጣ በማለም ከተለያዩ የፖለቲካ ቡድኖች ጋር በመመካከር ለውጥ ማምጣት ቢቻልም፣ በተለይ በአቶ ዳውድ ኢብሳ ከሚመራው የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ቡድን ጋር ዕርቅ ለማድረግ ተሞክሮ በሒደቱ ግን አሳዛኝ ክስተቶች ተፈጥረው ነበር ሲሉ አቶ ሽመልስ አስረድተዋል፡፡
ከአስመራ የመጣው የኦነግ ጦር ቀጥታ ወደ ካምፕ ቢገባም፣ በደቡብና በምዕራብ ኦሮሚያ ያለው እንቢ በማለቱ አሳዛኝ ጥፋቶች መከሰታቸውን አውስተዋል፡፡
ሆኖም እንቢ ያለውን ቡድን እነ አቶ ዳውድ ‹‹የእኛ አይደለም ሽፍታ ነው›› በማለታቸው በተወሰደ የሕግና የሰላም ማስከበር ሥራ፣ አካባቢዎቹ ወደ ቀድሞ እንቅስቃሴ መመለሳቸውንና የጦርነት ሥጋት እንደሌለባቸው ገልጸዋል፡፡ ሁሉም የአካባቢዎቹ መንገዶች ተከፍተው እንቅስቃሴዎች መጀመራቸውን በመግለጽም፣ አሁን እየተንቀሳቀሱ ጥቃት ከሚፈጽሙ ታጣቂ ቡድኖች ውጪ የጎላ ሥጋት የሚያደርስ ቡድን የለም ብለዋል፡፡
ከለውጡ ቀደም ብሎ በክልሉ ከፍተኛ ሕገወጥነት ይስተዋል እንደነበረ በመግለጽ፣ በተከናወነው የሕግና የፀጥታ ማስከበር ሥራ ሕገወጥነትን መከላከል መቻሉንና ወንጀል ቀንሶ ከፍተኛ መረጋጋት በክልሉ እንደመጣም ጠቁመዋል፡፡
በቅርቡ የአቶ ዳውድ ኦነግ በትጥቅ ትግል ላይ ያለ ማንኛውም ቡድን የእኛ ወገን አይደለም በማለት ከታጠቁት ጋር ራሱን መለየቱን፣ እንዲሁም በምዕራብ ኦሮሚያ ከሚንቀሳቀሰው የጃል መሮ ቡድን ከኦነግ ጋር በይፋ መለያየቱን አስታውቀው ነበር፡፡ ምዕራብ ኦሮሚያና ቤንሻንጉል ጉሙዝ አዋሳኝ አካባቢዎች አሁንም በኮማንድ ፖስት ከሚተዳደሩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚጠቀሱ ናቸው፡፡