የ2011 ዓ.ም. ያለ ምንም የወንጀል ድርጊት በሰላም መጠናቀቁን ፖሊስ ቢገልጽም፣ በአዲስ ዓመት መግቢያ ዋዜማ በተለያዩ አካባቢዎች ባልተያዙና በማይታወቁ ተሽከርካሪዎች አራት ሰዎች ተገጭተው መሞታቸው ታወቀ፡፡
የ2012 ዓ.ም. አዲስ ዓመት መቀበያ ዋዜማን ፖሊስ በገበያ ቦታዎችና በመዝናኛ ቦታዎች ከጳጉሜን 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ከኅብረተሰቡ ጋር በመሆን ጥብቅ ጥበቃ ማድረጉን የገለጸው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፣ ምንም ዓይነት የወንጀል ድርጊቶች እንዳልተፈጸሙ አስታውቋል፡፡
ነገር ግን በዋዜማው በአራዳ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሁለት ሰባራ ባቡር አካባቢ ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት አንድ ሰው፣ በተመሳሳይ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሦስት ከዮሐንስ ቤተ ክርስቱያን ወደ ጎጃም በረንዳ በሚወስደው መንገድ አቤት ሆስፒታል አካባቢ አንድ ሰው፣ በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ባልቻ ሆስፒታል አካባቢ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት አንድ ሰው፣ እንዲሁም በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሦስት መገናኛ አካባቢ አንድ ሰው በድምሩ አራት ሰዎች በተሽከርካሪ አደጋ ሕይወታቸው ማለፉን፣ የኮሚሽኑ ሕዝብ ግንኙነትና ኢንዶክትሪኔሽን ምክትል ዳይሬክተር ኮማንደር ፋሲካ ፈንታ አስረድተዋል፡፡
አደጋውን ያደረሱት ሁሉም ተሽከርካሪዎች ማምለጣቸውን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡ አደጋ አድርሰው የተሰወሩት ተሽከርካሪዎች ለጊዜው ባይያዙም፣ ፖሊስ እያደረገ ባለው ክትትል የተገኘ ምልክት ስላለ በቅርቡ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው እንደማይቀር አክለዋል፡፡
በዕለቱ 27 ከባድና ቀላል የንብረት ጉዳት አደጋዎች መድረሳቸውም ታውቋል፡፡ የ2011 ዓ.ም. መሸኛና የ2012 ዓ.ም. መቀበያ የበዓል ግርግር አደጋ እንዳይደርስ ፖሊስ ዕቅድ ነድፎ በመንቀሳቀሱ፣ ስኬታማ ሥራ ማከናወኑንና ኅብረተሰቡም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጉን ኮማንደር ፋሲካ ተናግረዋል፡፡
የትራፊክ አደጋ የብዙ ሰዎችን ሕይወት እየቀጠፈ በመሆኑ፣ አሽከርካሪዎች አደጋውን ለመቀነስ ብርቱ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸውም አሳስበዋል፡፡