የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ ፓርቲ (ኢዜማ) በአገር ውስጥ የጀመረውን አደረጃጀት ከማጠናክር ባለፈ፣ ከ70 በላይ በሚሆኑ አገሮች ኢትዮጵያውያን በሚኖሩባቸው ከተሞች መዋቅሩን ለመዘርጋት እየሠራ እንደሆነ አስታወቀ፡፡ በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን በአባልነት እንዲቀላቀሉት ጥሪውን አቅርቧል፡፡
ፓርቲው ይህን ያስታወቀው ዓርብ መስከረም 9 ቀን 2011 ዓ.ም. ‹‹ለኢትዮጵያ ተስፋ ከኢዜማ ጋር በጋራ እንሥራ›› በሚል ርዕስ ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ነው፡፡
ፓርቲው ከተመሠረተ ጀምሮ በአገር ውስጥ 400 በሚደርሱ የምርጫ ወረዳዎች አባላትና ደጋፊዎችን ማደራጀቱን ያስታወቀ ሲሆን፣ አሁን በመላው ዓለም የተጀመረው ሥራም፣ ‹‹ፓርቲው የጀመረውን ታላቅ አገራዊ ጥረት ለማገዝና በውጭ አገሮች የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን በአገራቸው ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ላይ ተገቢውን ተሳትፎ በማድረግ ለአገራቸው ዕድገት ገንቢ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ በማሰብ››፣ የኢዜማ ዓለም አቀፍ የድጋፍ ማኅበር ማቋቋም አስፈላጊ መሆኑን እንደሚያምን አስታውቋል፡፡
በዚህም መሠረት በመላው ዓለም ለሚገኙና የኢዜማ መሠረታዊ የፖለቲካ መርህ በሆነው ዜግነትን መሠረት ያደረገ ፖለቲካና በማኅበራዊ ፍትሕ የሚያምኑ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ፣ በየከተሞቹ በሚመሠረቱት የድጋፍ ማኅበራት አባል እንዲሆኑና ለአገራቸው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ከዚህ ቀደም ከስመው ኢዜማን በጋራ የመሠረቱ የፖለቲካ ድርጅቶች አባላትና ደጋፊዎች ለነበሩ፣ እንዲሁም በግልም ይሁን በአገር ደረጃ በነበሩ ማናቸውም ምክንያትና በፖለቲካ ውስጥ ያልተሳተፉ፣ ነገር ግን ኢዜማ የቆመላቸውን መርሆዎችን የሚደግፉ ኢትዮጵያውያን ፓርቲውን ተቀላቅለው እንዲታገሉ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
ኢዜማ አርበኞች ግንቦት 7፣ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲ ፓርቲ (ኢዴፓ)፣ ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ)፣ እንዲሁም የቀድሞ የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)ን ጨምሮ ራሳቸውን ባከሰሙ ሰባት ፓርቲዎች አማካይነት የተቋቋመ ፓርቲ መሆኑ ይታወሳል፡፡