የስፖርት አበረታች ቅመሞችን (ዶፒንግ) በዘላቂነት ለመከላከልና ለመቆጣጠር ይቻል ዘንድ፣ ከሁለት ዓመታት በፊት በወጣ ሕግ መሠረት ኢትዮጵያ እንቅስቃሴ እያደረገች ትገኛለች፡፡
መጋቢት 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የወጣውን የሚኒስትሮች ደንብ ቁጥር 400/2009 መነሻ በማድረግ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የፀረ አበረታች ቅመሞች ጽሕፈት ቤት ተቋቁሟል፡፡ ይህ ተቋም ሐሙስ፣ መስከረም 8 ቀን 2012 ዓ.ም. በጁፒተር ሆቴል ሁለተኛውን የፀረ አበረታች ቅመሞች የባለድርሻ አካላት ጉባዔ ባካሄደበት ወቅት፣ የተጠናከረ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ እንደሚጠበቅበት ተጠይቋል፡፡
በስፖርት ዘርፍ ፍትሐዊ የውድድር ሥርዓት መዘርጋትና በዓለም አቀፍ መድረኮች የኢትዮጵያን ውጤታማነት ብሎም ጤናማ ዜጎችን ማፍራት የመንግሥት ትኩረት እየሆነ መምጣቱ በተገለጸበት ጉባዔ፣ አገር አቀፍ ብሔራዊ ፌዴሬሽኖችና የሚመለከታቸው አካላት የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል፡፡
ጉባዔው በ2011 ዓ.ም. የነበረውን አጠቃላይ የውድድር እንቅስቃሴ ከመገምገመ በኋላ አቅጣጫዎች አስቀምጧል፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኖችን ጨምሮ በአጠቃላይ ከ110 ያላነሱ መንግሥታዊ ተቋማት፣ የሙያ ማኅበራትና ሌሎችም ተወካዮች በጉባዔው ተሳትፈዋል፡፡
በአበረታች ቅመሞች ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጹሑፎችና የምርምር ውጤቶች በቀረቡበት በዚሁ ጉባዔ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተቋቋመው የፀረ አበረታች ቅመሞች ጽሕፈት ቤት፣ ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በዓለም አቀፉ የፀረ አበረታች ተቋም (ዋዳ) ሪፖርት መሠረት ችግሩ ከታየባቸው አምስት የዓለም አገሮች ተርታ መካተቷን አስታውሷል፡፡ ይህንን ተከትሎም፣ ኢትዮጵያ ምንም እንኳ ከችግሩ ሙሉ በሙሉ መውጣት ባይቻላትም አሁን ላይ ጥሩ ለውጥ ማሳየቷን፣ ችግሩን ለመከታትልና ለመቆጣጠርም እየተወሰደ ባለው ዕርምጃ ሳቢያ ለሌሎች አገሮች በምሳሌነት ለመጠቀስ የበቃችበት ደረጃ ላይ መድረሷ በጉባዔው ተወስቷል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኖችም ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በመናበብ የሚጠበቅባቸውን ግዴታ እንዲወጡ የተጠየቁ ሲሆን፣ ሌሎች ባለድርሻዎችም ለዚህ አገራዊ ተልዕኮና የችግሩን አሳሳቢነት ግምት ውስጥ በማስገባት በባለቤትነት ስሜት እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ቀርቦላቸዋል፡፡