ሰሞኑን በተካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) 74ኛ ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የተገኙት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የዓባይን ወንዝ አጠቃቀም በዓለም አቀፍ መርህዎች ብቻ የተመሠረተ መሆን እንደሚገባው ኢትዮጵያ የፀና አቋም እንደምታራምድ፣ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድቡን የቴክኒክ ጉዳዮች ድርድሩ ለሚመለከታቸው ለሦስቱ አገሮች ባለሙያዎች ብቻ ሊተው እንደሚገባ አስታወቁ፡፡
ፕሬዚዳንቷ በአማርኛ ቋንቋ ለጠቅላላ ጉባዔው ባደረጉት ንግግር ግልጽ ካደረጉዋቸው የኢትዮጵያ መንግሥት አቋሞች መካከል፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብን የተመለከተው ይገኝበታል፡፡
የዓባይ ወንዝን የሚጋሩ አገሮች የረዥም ዘመናት ግንኙነትን ያዳበሩና በዚህ ወንዝ አማካይነትም እንዳይነጣጠሉ ሆነው መተሳሰራቸውን፣ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ አመላክተዋል፡፡
ኢትዮጵያ የዓባይ ውኃ አጠቃቀምን በዓለም አቀፍ መርሆች ማለትም የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም በፍትሐዊነት፣ በምክንያታዊነትና በሌሎች ላይ ጉልህ ጉዳት ባለማድረስ ሊሆን እንደሚገባ በፅኑ እንደምታምንና በዚህ እምነቷም በመመራት ከተፋሰሱ አገሮች ጋር 13 ዓመታት የፈጀ ድርድር በማድረግ፣ የዓባይ ውኃ አጠቃቀም ማዕቀፍ እንዲቀረፅ ማድረጓን አስታውሰዋል፡፡
የዓባይ ወንዝን ማዕከል ያደረገና ሕጋዊነት ያለው የባለ ብዙ ወገኖች መድረክ እንዲፈጠር ኢትዮጵያ አሁንም የምትፈልገው ቁርጠኛ አቋሟ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ሕዝብ 65 ሚሊዮን የሚሆነው በአሁኑ ወቅት የኤሌክትሪክ ኃይል አገልግሎት እንደማያገኝ ያወሱት ፕሬዚዳንቷ፣ በዓባይ ወንዝ ላይ የተጀመረው የኃይል ማመንጫ ግድብ፣ ‹‹እነዚህ ዜጎች ቢያንስ በኤሌክትሪክ ብርሃን ዓይተው መመገብ እንዲችሉ ዕድል የሚሰጥ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የህዳሴ ግድቡን መገንባት መጀመሯ በተፋሰሱ አገሮች መካከል የትብብር ዕድል የሚሰጥ እንጂ፣ የጥርጣሬና የውድድር ምንጭ ሊሆን እንደማይገባው አሳስበዋል፡፡
የግድቡን ግንባታ በተመለከተ በኢትዮጵያ፣ በግብፅና በሱዳን መካከል ከሦስቱም አገሮች በተወጣጡ ባለሙያዎች ድርድር በመካሄድ ላይ እንደሆነ ያስታወሱት ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ፣ ‹‹ቀሪ የቴክኒክ ጉዳዮች ድርድር ለባለሙያዎቹ ቡድን ሊተው ይገባል፤›› ብለዋል፡፡
በማከልም፣ ‹‹የዓባይ ወንዝ አጠቃቀምን በተመለከተ ከትብብር ውጪ ሌላ አማራጭ የለም፤›› ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ይህንን ንግግር ከማድረጋቸው ከሦስት ቀናት ቀደም ብሎ፣ የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ለተመድ ጠቅላላ ጉባዔ ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በዓባይ ላይ የምትገነባውን የህዳሴ ግድብ በተመለከተ የመንግሥታቸውን አቋም አስታውቀው ነበር፡፡
ፕሬዚዳንት አልሲሲ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ መገንባት የጀመረችው የህዳሴ ግድብ በግብፅ ላይ ጉዳት አለማድረሱን ለማረጋገጥ፣ እየተካሄደ ያለው ድርድር መጓተትና ውጤት አልባ መሆን እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል፡፡
በዚህ ምክንያም በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል፣ እንዲሁም በአጠቃላይ በአካባቢው አላስፈላጊ አለመረጋጋት ሊያስከትል እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
‹‹የዓባይ ውኃ ለግብፅ የሕይወትና የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ነገሮች ከመበላሸታው አስቀድሞ፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጣልቃ ሊገባ ይገባል፤›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት አልሲሲ ይህንን በሚናገሩበት ወቅት በግብፅ ካይሮ ከተማና በሌሎች ከተሞች፣ የእሳቸውን መንግሥት የሚቃወሙ ሕዝባዊ አመፆች ተቀስቅሰው በአሁኑ ወቅትም ሁኔታው ተባብሶ ቀጥሏል፡፡
የግብፅ ፕሬዚዳንት የህዳሴ ግድቡን በተመለከተ በድንገት ማራመድ የጀመሩት ከትብብር የመውጣት አቋም የገጠማቸውን ውስጣዊ የፖለቲካ ቀውስ ትኩረት ለማስቀየር እንደሆነ የኢትዮጵያ ውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሩ ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) መሰንበቻውን መግለጻቸው ይታወሳል፡፡