የሕዝብና ቤት ቆጠራው መካሄድ ባለመቻሉ ምክንያትና ሌሎች መረጃዎችም ባለመገኘታቸው ዘንድሮ እንዲሻሻልና ተግባራዊ እንዲደረግ ታቅዶ የነበረው የክልሎች የበጀት ድጎማ ማከፋፈያ ቀመር ማሻሻያ በሁለት ዓመት ተገፍቶ በ2015 ዓ.ም. ተግባራዊ እንዲደረግ ተወሰነ፡፡
ውሳኔውን ያሳለፈው የፌዴሬሽን ምክር ቤት መስከረም 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባካሄደው አምስተኛ ዓመት የሥራ ዘመን አንደኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው፡፡
በሥራ ላይ የሚገኘው የክልሎች የበጀት ድጎማ ማከፋፈያ ቀመር የፍትሐዊነት ጉድለት ያለበትና የጋራ ገቢዎች ክፍፍሉ ለፌዴራል መንግሥት የጎላ የተጠቃሚነት ድርሻ የሚሰጥ በመሆኑ፣ የማከፋፈያ ቀመሩ መሠረታዊ መርህዎች ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጅቶ ባለፈው ዓመት ተደጋጋሚ ውይይቶች ከክልል መንግሥታት ጋር ሲካሄድበት መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ይህ ማሻሻያ ረቂቅ በዚህ ዓመት ፀድቆ አዲስ የድጎማ በጀት ማከፋፈያ ቀመር ወደ ሥራ እንዲገባ ስምምነት ተደርሶ የነበረ ቢሆንም፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ማክሰኞ ዕለት ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው ቀመሩን ዘንድሮ አሻሽሎ ተግባራዊ ለማድርግ አስፈላጊ መረጃዎች ባለመገኘታቸው፣ በሥራ ላይ የሚገኘው ቀመር ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት እንዲቀጥል ወስኗል፡፡ ቀመሩ የሚፈለጉ መረጃዎችን መሠረት በማድረግ ተሻሽሎ በ2015 ዓ.ም. ተግባራዊ እንዲደረግ በቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ላይ ሰፊ ክርክር ከተካሄደ በኋላ፣ በበርካታ ተቃውሞ በአብላጫ ድምፅ ፀድቋል፡፡
ቀመሩን ለማሻሻል አዲስ ከሚካሄደው የሕዝብና ቤት ቆጠራ የሚገኝን የሕዝብ መጠን መረጃ መሠረት አድርጎ እንዲቀረጽ ታሳቢ የተደረገ ቢሆንም፣ በአገሪቱ በተከሰቱ አለመረጋጋቶች ቆጠራውን ለማካሄድ ባለመቻሉ መረጃውን ማግኘት እንዳተቻለና በዘንድሮ ዓመትም አገር አቀፍ ምርጫ ተደርቦ በመምጣቱ ቀመሩን ለማሻሻል ምቹ ባለመሆኑ ለሁለት ዓመት እንዲራዘም የውሳኔ ሐሳብ ቀርቧል፡፡
የቀመሩ ማሻሻያና ትግበራ ለሁለት ዓመት እንዲራዘም በቀረበው ውሳኔ ሐሳብ ላይ የተጠቀሱት ምክንያቶች አሳማኝ አለመሆናቸውን በመጥቀስ በርከት ያሉ የምክር ቤቱ አባላት ጥያቄ አንስተዋል፡፡
ከእነዚህም መካከል የአማራ ክልልን የወከሉት የምክር ቤቱ አባልና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ሕዝብና ቤት ቆጠራው ባለመካሄዱ ተፈላጊው መረጃ አልተገኘም በሚል የቀረበው ምክንያት በቂና አሳማኝ ባለመሆኑ ያለውን የሕዝብ መጠን ትንበያ መረጃ በመጠቀም ማሻሻያው ሊከናወን እንደሚገባ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ይሁን እንጂ ጉዳዩ የሚመለከተው የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ ቀመሩን ለማሻሻል የሚፈለገው ጠቃሚ መረጃ የሕዝብ ቁጥር ብቻ እንዳልሆነ አመልክቷል፡፡
ሌሎች ተፈላጊ ከሆኑት መረጃዎች መካከል ወቅታዊ የሆኑ የድህነት ምጣኔ መረጃና አገር አቀፍ የዋጋ ምጣኔ መረጃ አለመኖራቸው ተጨማሪ ምክንያቶች መሆናቸውን ተጠቅሷል፡፡
በመሆኑም የሕዝብና ቤት ቆጠራ በመራዘሙ እንዲሁም ዘንድሮ አገራዊ ምርጫ የሚካሄድበት ዓመት በመሆኑ፣ አዲሱን ቀመር የፌዴራልና የክልል አመራሮችን አግኝቶ አሳታፊ በሆነ መንገድ ለማዘጋጀት አስቸጋሪ ስለሚሆን ለሁለት ዓመት እንዲገፋ የቀረበው ሐሳብ በበርካታ ተቃውሞ በአብላጫ ድምፅ ፀድቋል።
የሕዝብና ቤት ቆጠራ ሁለት ጊዜ ተራዝሞ 2012 ዓ.ም. እንዲካሄድ ባለፈው ዓመት መወሰኑ የሚታወስ ቢሆንም፣ ዘንድሮ የመካሄዱ ነገርም አጠራጣሪ ሆኗል፡፡ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ባለፈው ሰኞ መስረም 26 ቀን 2012 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች የሥራ ዘመን መክፈቻ የጋራ ስብሳባ ላይ ባደረጉት ንግግር የዓመቱን የመንግሥት ትኩረቶች ሲገልጹ፣ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ስለመካሄዱ አልጠቆሙም ወይም ያሉት ነገር የለም፡፡