Sunday, June 4, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ኪንና ባህልየሥነ ትምህርትና ሥነ ልቦና ልሂቅ አግደው ረዴ አግደው (ዶ/ር) (1932-2012)

የሥነ ትምህርትና ሥነ ልቦና ልሂቅ አግደው ረዴ አግደው (ዶ/ር) (1932-2012)

ቀን:

በኢትዮጵያ ዘመናዊ ትምህርት ጉዞ በየዐረፍተ ዘመኑ ከሚጠቀሱትና ከሚወሱት ልሂቃን መካከል አንዱ አግደው ረዴ አግደው (ዶ/ር) ናቸው፡፡ በአካዴሚያው በሥነ ትምህርትና በሥነ ልቦና እስከ ዱክትርናው የትምህርት ጫፍ ደርሰዋል፡፡

አገራዊ አገልግሎታቸው የሚነሳው በኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ዘመን በትምህርትና ሥነ ጥበብ ሚኒስቴር የሚኒስትሩ አማካሪና የፕላን ቺፍ ኤክስፐርት ሆነው በመሥራት ነበር፡፡ ከዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ዳይሬክተርነት ባለፈ፣ ከኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲንነት እስከ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከባንኪንግ ኢንስቲትዩት እስከ የኢትዮጵያ ቤተሰብ መምሪያ የትምህርት ሳይኮሎጂ፣ የካውንስሊንግ ሳይኮሎጂ በማስተማር፣ በማማከርና በምርምር ዘርፍ በርካታ ሥራ ሠርተዋል፡፡

በዘውዳዊው ሥርዓት ‹‹የትምህርት ፍቱን መድኃኒትነት በሥራ መግለጽ ነው›› የሚል መሪ ቃል የነበረው በርካታ አገራዊ አገልግሎት በዘመኑ ያበረከተው፣ ‹‹የኢትዮጵያ ወጣቶች አገልግሎት›› (Ethiopian Youth Service)  ከመሠረቱት ታዋቂ ባለሙያዎች አንዱ አግደው ረዴ (ዶ/ር) ነበሩ፡፡

በትምህርት ሚኒስቴር ፕላንና ምርምር ከፍተኛ ኤክስፐርትም ሆነው የኢትዮጵያ የትምህርት አቅጣጫና ሥርዓት ትምህርት አደራጅና ተመራማሪ በመሆንም ያገለገሉ ሲሆን የከፍተኛ ትምህርት ኮሚሽን የምርምርና የውጭ ግንኙነት ኃላፊ በመሆን ሠርተዋል፡፡ የአምቦ፣ የጅማ፣ የዓለማያ፣ የጎንደር፣ የመቐለ፣ የድሬዳዋና ሌሎችም ኮሌጆች ዩኒቨርሲቲዎች ማስፋፊያዎች ላይ የነበራቸው አስተዋፅኦ ተጠቃሽ ነው፡፡ በውጭ ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴርም የአውሮፓና የአሜሪካ አገሮች ትብብር መምርያ ኃላፊም ነበሩ፡፡

ከሦስት አሠርታት ግድም በፊት የተቋቋመውና የኢትዮጵያን ጥንታዊ ቅርሶች ለመጠበቅና ከአደጋ ለመታደግ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ቅርስ ባለአደራ ማኅበር ከመሥራች አባልነት ባሻገር የቦርድ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው አገልግለዋል፡፡

በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች፣ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች፣ በቤተ ክርስቲያን በግል ማማከሪያ ተቋማት፣ በፋይናንሻል ድርጅቶች፣ በምርምርና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ ወዘተ. ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡

በቦርድ አባልነትና በሊቀ መንበርነት ካገለገሉባቸው ውስጥ በኮንሰርቲንግ ኦፍ ክርስቲያን ሪሊፍ ኤንድ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን (በሲሲአርዲኤ) የቦርድ አባል፣ በኢትዮጵያ የእምነት ተቋማት ፎረም (ኤፍዳ) የቦርድ አባል፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን የቦርድ አባል፣ ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የቦርድ አባል፣ በኢትዮጵያ ቤተሰብ መምርያ የቦርድ አባል፣ በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል የቦርድ አባል፣ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለአደራ ማኅበር መሥራችና የቦርድ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው አገራዊ ግዴታቸውን ተወጥተዋል፡፡

የሥነ ትምህርትና ሥነ ልቦና ልሂቅ አግደው ረዴ አግደው (ዶ/ር) (1932-2012)

 

ዶ/ር አግደው ገጸ ታሪካቸው እንደሚያስረዳው፣ በተጓዳኝ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት ክፍሎች የፒኤችዲ እና የማስትሬት ዲግሪ ማሟያ በርካታ የምርምር ጽሑፎችን በፈታኝነት አገልግለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት በኮሙዩኒኬሽንና በግጭት አፈታት መምህር በመሆን ከማገልገላቸውም በላይ በተለያዩ አገር አቀፍ፣ አኅጉር አቀፋዊ፣ የምርምርና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በትምህርት፣ በሳይኮሎጂ፣ በፋይናንስ፣ በኅብረተሰብ ዕድገት፣ ከ25 በላይ የምርምር ጽሑፎችን አበርክተዋል፡፡

በጀርመን ቴክኒካል ተራድኦ ድርጅት ድርጅት (ጂ.አይ.ዜድ) የገጠር ልማቶች ማኅበራት ጥናት አደራጅ፣ የአግደው ረዴና ተባባሪዎች የትምህርት ምርምር ተቋም መሥራችና ዋና ዳይሬክተር ሆነው ለበርካታ ዓመታት ከማገልገላቸውም በላይ፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ኮሚሽነርነት ለበርካታ ዓመታት ዜና ዕረፍታቸው እስከ ተሰማበት ጊዜ አገልግለዋል፡፡

ከእናታቸው ከወይዘሮ ጎጃም ላንቺ አፍራሽና ከአርበኛው አባታቸው ከልጅ ረዴ አግደው በጎጃም ጠቅላይ ግዛት፣ በደጀን ወረዳ በደጀን ጊዮርጊስ ልጥጥ በምትባል ልዩ መንደር ኅዳር 24 ቀን 1932 ዓ.ም. የተወለዱት ዶ/ር አግደው፣ የመጀመርያና ሁለተኛ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ተከታትለዋል፡፡

በእንግሊዝ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲና በከሊሃም ኮሌጅ በኮምፓራቲቭ ኢዱኬሽን የመጀመርያ ዲግሪያቸውን (1957)፣ በኒው ዮርክ ሲቲ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ በካውንስሊንግ ሳይኮሎጂ በማስተር ኦፍ አርትስ (1961)፣ ሁለተኛ የማስትሬት ዲግሪያቸውን  በኢንተርናሽናል ኢዱኬሽን ፕላኒንግ (1967) በተመሳሳይ ዩኒቨርሲቲ ጨርሰዋል፡፡ የፒኤችዲ ዲግሪያቸውን በአፕላይድ ሂዩማን ዴቨሎፕመንትና ጋይዳንስ ሳይኮሎጂ (1970) አጠናቀዋል፡፡

ሐምሌ 24 ቀን 1957 ዓ.ም. ከወይዘሮ ቆንጂት ታደሰ ጋር ጋብቻ ፈጽመው አራት ሴቶች ልጆችና አንድ ወንድ ልጅ፣ አሥር የልጅ ልጆችና ሁለት የልጅ ልጅ ልጅ ያፈሩት ዶ/ር አግደው፣ መስከረም 29 ቀን 2012 ዓ.ም. ሥራ ውለው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲመለሱ በተወለዱ በ80 ዓመታቸው በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡

የነፍስ ኄር / አግደው ረዴ ሥርዓተ ቀብር ቅዳሜ ጥቅምት 1 ቀን በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ዘጠኝ ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ የሥራ ባልደረቦቻቸው፣ ወዳጅ ዘመድና አንድ ሺዎች በተገኙበት ተፈጽሟል። አንዳንዶች በሥርዓተ ቀብሩ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት ሹማምንት አለመገኘታቸው ለምን ሲሉ ተደምጠዋል፡፡

 “ባረፉ አርቲስቶች ቀብር ለመገኘት የሚተጉት ሹማምንት ተወካዮች ተገኝተው ቢሆን ኖሮ፣ ድምፃቸውን አሰምተው ቢሆን ኖሮ፤የፊት ወዳጅህን በምን ቀበርከው በሻሽ የኋላው እንዳይሸሽየሚለውን ባልተረትንም ሲሉ ተሰምተዋል።

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

አወዛጋቢው የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ጉዳይ

በኢትዮጵያ የሕገ መንግሥት ማሻሻል ጉዳይ ከፍተኛ የፖለቲካ ውዝግብ የሚቀሰቀስበት...

 መፍትሔ  ያላዘለው  የጎዳና  መደብሮችን  ማፍረስ

በአበበ ፍቅር ያለፉት ስድስት ዓመታት በርካቶች በግጭቶችና በመፈናቀሎች በከፍተኛ ሁኔታ...

የተናደው ከቀደምቱ አንዱ የነበረው የአዲስ አበባ ታሪካዊ ሕንፃ

ዳግማዊ አፄ ምኒልክ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ መናገሻ ከተማቸውን...

የአከርካሪ አጥንት ሕክምናን ከፍ ያደረገው ‘ካይሮፕራክቲክ’

በአፍሪካ ከጀርባ ሕመም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች ለከፍተኛ የአካል...