ጥቅምት 10 ቀን 2012 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ተገኝተው በፌዴራል ፖሊስ ተይዘው በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በአደራ ቁጥጥር ሥር የሚገኙት ተጠርጣሪ ታሳሪዎችን የጎበኙት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) ከ300 በላይ ታሳሪዎችን የያዘው የወንዶች እስር ቦታ እጅግ የተጨናነቀ፣ በውኃ መቆራረጥና በታሳሪዎች ብዛትም የፅዳት ደረጃው ዝቅተኛ እንደሆነ አስታወቁ፡፡
ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በባህር ዳርና በአዲስ አበባ ከተሞች ከተፈጸሙ የባለሥልጣን ግድያዎች ጋር በተያያዘና በሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮች በቁጥጥር ሥር ከሚገኙ እስረኞች ውስጥ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አመራርና አባላት፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባላት፣ የኢትኦጲስ ጋዜጣ ባልደረቦች፣ ‹‹የተጠለፈው ትግል›› ከሚለው መጽሐፍ ኅትመት ጋር በተያያዘ በእስር የሚገኙትን ተጠርጣሪዎችን፣ እንዲሁም የሟች ብርጋዴር ጄኔራል አሳምነው ፅጌ ባለቤት ወ/ሮ ደስታ አሰፋንና ሌሎች ታሳሪዎችን ከማነጋገር በተጨማሪ፣ ጉዳያቸው ያለበትን ደረጃና የእስር ሁኔታም ተመልክተዋል፡፡
በዚህም መሠረት የሴቶቹ የእስር ክፍል በአንፃራዊነት የተሻለና የፅዳት ደረጃው የተጠበቀ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ የወንዶቹ ግን መሻሻል የሚያስፈልገው ነገር እንዳለ አስታውቀዋል፡፡
‹‹ታሳሪዎቹ ከሦስት እስከ አራት ወራት ያህል የፖሊስ ምርመራን ለማጠናቀቅ በሚል በእስር የቆዩ፣ በአሁኑ ወቅት በሕግ የሚፈቀደው የተጨማሪ ምርመራ ጊዜ በአብዛኛው የተጠናቀቀና ቀሪውም በመጠናቀቅ ላይ ያለ በመሆኑ፣ ከዚህ በላይ ታሳሪዎቹ በእስር ሊቆዩ ስለማይገባ እንደ አግባቡ በዋስ ወይም ያለ ዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ ወይም ተዓማኒ የሆነ ክስ በመደበኛው የወንጀል ሕግ መሠረት ሊቀርብ ይገባል፤›› ሲሉ ኮሚሽነሩ አሳስበዋል፡፡
‹‹ከአንድ መጽሐፍ ኅትመት ጋር በተያያዘ የመጽሐፉ ጸሐፊ ነው ተብሎ ከተጠረጠረ ግለሰብ አንስቶ የማተሚያ ቤቱ ባለቤት፣ የመጽሐፉን የፊት ገጽ ዲዛይን የሠራ ግለሰብ፣ የመጽሐፉ አከፋፋይና የመጽሐፉ የጎዳና ላይ ቸርቻሪ ሻጭ ሳይቀር፣ እንዲሁም ሌሎች ታሳሪዎች ፍርድ ቤት በሚቀርቡበት ጊዜ ፎቶ አንስተሀል በሚል የተያዘ ጋዜጠኛን ጭምር ለዚህን ያህል ጊዜ በእስር መቆየታቸው አሳሳቢ ሁኔታ በመሆኑ፣ አፋጣኝ እልባትና የዋስትና መብት መከበር ያስፈልገዋል፤›› ሲሉ ለጉዳዩ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጠው ለሚመለከተው አካል ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ዋና ኮሚሽነሩ ከዚህ ቀደም ከመስከረም 7 እስከ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. በሐዋሳ ከተማ የሥራ ጉብኝት አድርገው የነበረ ሲሆን፣ በወቅቱም በሐምሌ ወር 2011 ዓ.ም. ከሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄ ጋር ተያይዞ በተነሳው ግጭት ምክንያት በፖሊስ ቁጥጥር የሚገኙ ተጠርጣሪ እስረኞችን መጎብኘታቸው የሚታወስ ነው፡፡