በተመስገን ተጋፋው
በአጠቃላይ ትምህርት ዘርፍ ከ5ኛ እስከ 12ኛ ክፍል የርቀት ትምህርትን ለመተግበር ረቂቅ መመርያ ተዘጋጅቶ ውይይት ተደረገበት፡፡
መንግሥት መደበኛና መደበኛ ያልሆኑ የትምህርት ፕሮግራሞችን በመዘርጋትና ዜጎች የትምህርት ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል ካስቀመጣቸው መርሐ ግብሮች አንዱ የርቀት ትምህርት ሲሆን፣ መርሐ ግብሩም ከዚህ ቀደም በተለያዩ የመንግሥትና የግል ተቋማት ሲተገበር ቆይቷል፡፡
ሆኖም ወጥነት ባለውና በአገር አቀፍ ደረጃ ለመተግበር፣ የትምህርት ጥራቱን ለመከታተል በሚያመች ሁኔታ በአጠቃላይ የትምህርት ዘርፍ ከአምስተኛ እስከ 12ኛ ክፍል የርቀት ትምህርት ማስተግበሪያ ረቂቅ መመርያ መዘጋጀቱን ትምህርት ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
የረቂቁ ማስተግበሪያ ማንዋል ስለ ርቀት ትምህርቱ ተጠቃሚዎች፣ የሞጁል አዘገጃጀት፣ ማጠናከሪያ ትምህርት መስጫ ማዕከላት አደረጃጀትና ትምህርት አሰጣጥ፣ የምዘና ሥርዓት፣ የተማሪዎች ምዝገባ፣ ሪከርድ አያያዝ፣ የሚመለከታቸው አካላት ተግባርና ኃላፊነት እንዲሁም የተቋማት ፈቃድ አሰጣጥና ስረዛን በተመለከተ በውስጡ መካተቱን ለማሳወቅ ከክልሎች ከተውጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎች ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡
ረቂቅ ሰነዱ በቀጣይም ከባለሙያዎችና ከተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች ጋር ውይይት የሚደረግበት ሲሆን፣ ፀድቆም ወደ ተግባር እንደሚገባ የሚኒስቴሩ የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት አስታውቋል፡፡