የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ችግር ዘላቂ ሰላም የሚያገኘው ያሉት የፖለቲካ ኃይሎች ሁሉ ችግሩን በተመለከተ ቁጭ ብሎ በመነጋገር፣ በመወያየት፣ ባለፉት ታሪኮች፣ ዛሬ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች፣ እንዲሁም በወደፊቱ መስማማት፣ መረዳዳትና መተማመን በመካከላቸው በመፍጠር ብቻ መሆኑን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አስታወቀ፡፡ ከፓርላማ ኃይሎች ጋርም አብሮ ለመሥራት እንደሚፈልግ ገለጸ፡፡
ኦነግ ይህን አቋሙን ይፋ ያደረገው ‹‹የመልካም ግንኙነት ጥሪ ለሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች›› በሚል ርዕስ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ ነው፡፡ ኦነግ በመግለጫው የግልጽ ውይይትን ጠቃሚነትና አስፈላጊነት በማውሳት፣ ለሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በጉዳዩ ላይ የአብረን እንሥራ ጥሪውንም አስተላልፏል፡፡
ኦነግ በዚህች አገር የወደፊት የፖለቲካ ሒደት ውስጥ የሕዝቦች ነፃነት፣ እውነተኛ ዴሞክራሲ፣ ዘላቂ ሰላምና ዕድገት ዕውን ለማድረግ ይረዳ ዘንድ ካሉት ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በመነጋገር፣ በመወያየት፣ በሚያግባቡ ጉዳዮች ላይ በመተማመን አብሮ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑንም አስታውቋል፡፡
በአገሪቱ የሚታዩ የፖለቲካ አመለካከቶች ልዩነት በሰከነና በሠለጠነ መንገድ መፍታት እንደሚገባ የገለጸው ኦነግ፣ ‹‹አንዱ ወገን ሌላውን በኃይል ደፍጥጦና አፍኖ ዕልባት ያገኛል ብሎ ማሰብ ከከንቱ ህልምና ምኞት የሚያልፍ አይመስለንም፤›› በማለት፣ አብሮ በጋራ መሥራት ወሳኝ መሆኑን በአጽንኦት አስታውቋል፡፡
‹‹በቃላት ድለላና የተስፋ ዳቦ ብቻ በይቅርታና በዕርቅ ስም ወይም የአብሮነትን ጥቅም መስበክና ማወደሰን በመሳሰሉት ብቻ የሚፈለገውን ዕርቅ፣ የሕዝቦች ነፃነትና አብሮነት፣ ዴሞክራሲ፣ ዘላቂ ሰላምና ዕድገት ይመጣሉ ብሎ መመኘት ከምኞት ያልፋል ብሎ ማመንም ይከብዳል፤›› ሲል፣ ከቃላት ያለፈ ተግባራዊ ሥራዎች መከናወን እንደሚገባቸው አሳስቧል፡፡
ወቅታዊ የአገሪቱ ፖለቲካዊ ችግር ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ገዝፎኖ አሥጊ ሆኖ እንደሚታይ የገለጸው ኦነግ፣ ‹‹በሕዝቦች ትዕግሥትና መስዋዕትነት የተጀመረውን የለውጥ ጅማሮ ደግፎ የለውጡም አካል ሆኖ ለማስቀጠል ቃል ገብቶ ሥልጣኑን የተረከበው የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አስተዳደር፣ እየታዩ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት እያከናወናቸው ያሉ ሥራዎች እንዳሉ ሆነው የተለያየ አመለካከት ያላቸው የፖለቲካ ኃይሎች በመደማመጥ ለአገርና ለሕዝቦች ሰላም ሲባል መወያየትና በሚቻለው ላይ ደግሞ መተጋገዝ ወሳኝ ነው፤›› በማለት፣ የአብሮን እንሥራ ጥሪውን ለሁለም የፖለቲካ ኃይሎች አስተላልፏል፡፡