በኡጋንዳ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የዘንድሮው የምሥራቅና መካከለኛው አፍሪካ አገሮች ዋንጫ (ሴካፋ) ተሳታፊ አገሮች ራሳቸውን ከውድድሩ እያገለሉ ነው፡፡ ኢትዮጵያና ሩዋንዳ ‹‹በበጀት እጥረት›› በሚል ሁለቱም ከሻምፒዮናው ተሰናብተዋል፡፡ ውድድሩ ከኅዳር 27 እስከ ታኅሣሥ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. በሩዋንዳ ኪጋሊ እንደሚካሄድ ይጠበቃል፡፡
ቀደም ብላ ራሷን ከሴካፋ እንዳገለለች ያስታወቀችው ሩዋንዳ፣ በቅርቡ ለሚካሄደው የአፍሪካ አገሮች ዋንጫ (ቻን) ማጣሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ተጫውታ በደርሶ መልስ ውጤት አሸናፊ ሆና በካሜሮን ለሚዘጋጀው ቻን መብቃቷ አይዘነጋም፡፡ በዚህም ሁለቱ አገሮች የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች በሚደለደሉበት ሴካፋ ውድድር ላለመሳተፍ የገንዘብ ችግር እንደ ምክንያት ማቅረባቸው አጠያይቋል፡፡
በሌላ በኩል ዞኑ በተደጋጋሚ የሚቀርብበት ቅሬታ፣ የሴካፋ አገሮች ውድድር በመደበኛነት ወቅቱን ጠብቆ የማይካሄድ፣ ከፍተኛ የሆነ የመርሐ ግብር መፋለስና ወጣገባነት የሚበዛበት መሆኑ ይወሳል፡፡ እንዲሁም በዞኑ የሚመደቡ አገሮች ለውድድሩ የሚሰጡት ትኩረትና የገንዘብ አስተዋጽኦ ታክሎበት ሴካፋ ከውጤታማነቱ ይልቅ በአገሮቹ ላይ የጫና ውድድር ተደርጎ መታየቱ ለተሳትፎው መዳከም በዋና ምክንያት ይጠቀሳል፡፡
የመርሐ ግብሩ ደካማ መሆን፣ አገሮች ለዞኑ እግር ኳስ ዕድገት ብዙም የማይመርጡት እየሆነ በመምጣቱ ጭምር ተሳታፊ አገሮች ሰበብ እየደረደሩ ከተሳትፎ ገሸሽ የሚሉበት እየሆነ መጥቷል፡፡ ከአፍሪካ እግር ኳስ አምስቱ ዞኖች አንዱ የሆነው ሴካፋ፣ ከመጪው ቅዳሜ ጀምሮ በሩዋንዳ ኪጋሊ 12 አገሮች በሦስት ምድብ ተከፋፍለው የሚያደርጉት ሻምፒዮና ነው፡፡
የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች በእግር ኳሱ ብቻ ሳይሆን፣ በብዙ መልኩ በደካማነቱ ተጠቃሽ ነው፡፡ በኡጋንዳ እንዲካሄድ ድንገተኛ መርሐ ግብር ተይዞለት የቆየው ሴካፋ፣ በምድብ አንድ አስተናጋጇ ኡጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ኢትዮጵያና ኤርትራ ሲገኙ፤ በምድብ ሁለት ደግሞ ዴሞክራቲክ ኮንጎ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳንና ሶማሊያ ተመድበዋል፡፡ በምድብ ሦስት ኬንያ፣ ታንዛኒያ፣ ጅቡቲና ዛንዚባር ተደልድለው የነበረ መሆኑ ይታወቃል፡፡
የበጀት እጥረት ምክንያት አድርጎ ከሴካፋ ሻምፒዮና ራሱን ያገለለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) እ.ኤ.አ በ2021 ለሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ አይቮሪኮስት፣ ማደጋስካርና ኒጀር በሚገኙበት ምድብ ተደልድሎ ማጣሪያውን ጀምሯል፡፡ በቅርቡ ምዕራብ አፍሪካዊቷን ጠንካራ የእግር ኳስ አገር አይቮሪኮስትን በሜዳው አስተናግዶ 2ለ1 በሆነ ውጤት ማሸነፉ ይታወሳል፡፡
አንዳንድ ሙያተኞች የፌዴሬሽኑ ውሳኔ ትክክል እንዳልሆነ የሚናገሩ አልጠፉም፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የወቅቱ ዋና አሠልጣኝ ኢንስትራክተር አብርሃም መብርሃቱ በተደጋጋሚ እንደሚናገሩት የቡድናቸው ስብስብ ዘጠና አምስት በመቶ ወጣቶች በመሆናቸው ኢንተርናሽናል የወዳጅነት ጨዋታ እንደሚያስፈልጋቸው ነው፡፡
ሴካፋ ምንም እንኳን በደካማነት ቢወሳም በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ኡጋንዳና ኬንያ እንዲሁም ቀደም ብላ ከሴካፋ ራሷን ያገለለችው ሩዋንዳ የመሳሰሉት አገሮች እግር ኳሳቸው ባልተጠበቀ ፍጥነት እያደገ መሆኑ ይታያል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከእነዚህ አገሮች ጋር ሴካፋን ምክንያት አድርጎ ተሳትፎ ቢያደርግ ዋና አሠልጣኙ እንደ ክፍተት ለሚያነሱት ሰበብ ምላሽ ሊሆን እንደሚችል ጭምር የሚያስረዱ አልጠፉም፡፡