ካለፈው ወር ጀምሮ በምሥራቅ አፍሪካ መጣል የጀመረው ከባድ ዝናብ ያስከተለው ጎርፍ ከ50 በላይ ሰዎች እንዲሞቱና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ ምክንያት ሆኗል፡፡
የአየር ንብረት ለውጥ ተመራማሪዎች የህንድ ውቅያኖስ መሞቅ የምሥራቅ አፍሪካን የዝናብ ሥርዓት ሊያዛባው እንደሚችል ቀድመው አስጠንቅቀው ነበር፡፡
በደቡብ ሱዳን በባያፖር ከተማ ባለፈው ወር በተከሰተ ጎርፍ 420 ሺሕ ሰዎች ከመንደራቸው ተፈናቅለዋል፡፡
የምዕራብ ህንድ ውቅያኖስ ከዚህ ቀደም በተለየ መልኩ ሙቀቱ የጨመረ ሲሆን፣ ይህ ያስከተለው ትነት በአፍሪካ ቀንድ ወቅቱን ያልጠበቀና ከባድ ዝናብ እንዲጥል አድርጓል፡፡ የውቅያኖሱ መሞቅም ሊተነበይ የማይችል አየር ንብረት ሊያስከትል እንደሚችልም ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ከኢንዱስትሪዎች መስፋፋትና፣ ከደን መጨፍጨፍና ግሪን ኢኮኖሚን በአግባቡ ካለመተግበር ጋር ተያይዞ የተከሰተው የአየር ንብረት ለውጥ በተለይ በአፍሪካ የሚገኙ ደሃ አገሮችን እንደሚጎዳ በውቅያኖስ ላይ የተከሰተው ከመጠን ያለፈ ሙቀት፣ ባለፈው 100 ዓመት በየአሥር ዓመቱ 0.13 ዲግሪ ሴንቲግሬድ እንዲጨምር ምክንያት መሆኑን የአሜሪካ ብሔራዊ የውቅያኖስ አየር አስተዳደር አስታውቋል፡፡
የህንድ ውቅያኖስ ከ1970ዎቹ ጀምሮ የግሪን ሃውስ ጋዝ ልቀትን 93 በመቶ እንደሚመጥ ተመራማሪዎች ገልጸው፣ ይህም ብዙ እንደሆነና በዚህ ሳቢያ የሚፈጠረው ሙቀት የሚፈጥረው ትነት በተለይ ምሥራቅ አፍሪካን ላልተጠበቀ ከባድ ዝናብ እንደሚያጋልጣት ጠቁመዋል፡፡
ኢትዮጵያ ሰሞኑን ያልተጠበቀ ዝናብ አስተናግዳ በጋምቤላና በአንዳንድ አካባቢዎች የደረሱ ሰብሎች ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ አርሶ አደሮች ሰብላቸውን እንዲሰበስቡ ጥሪ ተደርጎም፣ የደረሱ ሰብሎች ተሰብስበዋል፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ ዝናቡን አፈናው ሰብሉን ለማንሳት ዕድል አልሰጠም፡፡ ለተከታታይ ቀናት ጨፍግጎ የያዘው ዝናብ አርሶ አደሩን ማሳውን እንዲያድንም አድርጓል፡፡
ኬንያ ደግሞ ከባድ የተባለውን ዝናብ ያስተናገደችው ሰሞኑን ነው፡፡ በጎርፍ 250 ሰዎች ሲሞቱ፣ 17ሺሕ ደግሞ ተፈናቅለዋል፡፡
በደቡብ ሱዳን በባይፖር በተከሰተ ጎርፍ የገበያ ሥፍራዎች፣ ትምህርት ቤቶች፣ መኖሪያ ቤቶችና የከብት በረቶች ተውጠዋል፡፡ በአካባቢው ከዚህ ቀደም ከተከሰተ ጎርፍ የከፋ እንደነበርም ሮይተርስ አስፍሯል፡፡
በሶማሊያ ወንዞች ሞልተው በመፍሰሳቸው 370 ሺሕ ሰዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል፡፡ እርሻዎችም ወድመዋል፡፡ 17 ሰዎች ደግሞ ሞተዋል፡፡
በምሥራቅ አፍሪካ ከባድ ዝናብና ጎርፍን በአውስትራሊያ ደግሞ ድርቅን ያስከተለው የህንድ ውቅያኖስ መሞቅ፣ የአፍሪካ ቀንድ አገሮች ከዚህ ቀደም ከነበረው በተለየ መልኩ ቀዝቃዛ እንዲሆኑ እንደሚያደርግም ቢቢሲ አስፍሯል፡፡
በአጭር ጊዜ ውስጥ የአፍሪካ ቀንድ አገሮች ብርቱ ቅዝቃዜን እንደሚያስተናግዱ፣ በተያዘው ወርም በደቡብ ምሥራቅ ኬንያና በታንዛኒያ፣ በማላዊና በሰሜናዊ ዛምቢያ ከባድ ዝናብ እንደሚጥልም ተገልጿል፡፡
በቅርብ ዓመታት በተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተው ጎርፍ
ቢቢሲ ኦቻን ጠቅሶ እንዳሰፈረው፣ በቅርብ ዓመታት ውስጥ በአፍሪካ ቀንድ፣ በማዕከላዊ አፍሪካና ምሥራቅ አፍሪካ የተከሰተ ጎርፍ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን ጎድቷል፡፡
በደቡብ ሱዳን 908 ሺሕ፣ በማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ 100 ሺሕ ሰዎች እንዲፈናቀሉ፣ በኡጋንዳ ደግሞ 3,800 ሰዎች እንዲፈናቀሉና ስድስት እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል፡፡
በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ 200 ሺሕ ሲፈናቀሉ፣ 40 ሞት ተመዝግቧል፡፡ በሱዳን 426 ሺሕ ሲጎዱ፣ በጂቡቲ 150 ሺሕ ተጎድተው ዘጠኝ ሞተዋል፡፡
በኢትዮጵያ 570 ሺሕ በጎርፍ የተጎዱ ሲሆን፣ 23 በሶማሊያ 547 ሺሕ በጎርፍ ተጠቅተዋል፣ 17 ሞተዋል፡፡ በኬንያ 160 ሺሕ በጎርፍ ችግር ውስጥ ሲወድቁ፣ 120 ሞት ተመዝግቧል፡፡ በታንዛኒያ ደግሞ 1,100 ተጎድተው 44 መሞታቸውን የቢቢሲ መረጃ ያሳያል፡፡