በአሥራ ሰባተኛው ክፍለ ዘመን የመጀመርያው ሩብ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት የነበሩት አፄ ሱስንዮስ መልዐክ ሰገድ (1558 –1625 ዓ.ም.) ማዕከላቸው ደምቢያ ጎርጎራ ነበር፡፡ ልጃቸው ፋሲለደስ ተተክተው ጎንደር እስኪመሠረቱ ድረስ የጎርጎራ መዲናነት አልተለየም፡፡
ከጎርጎራ ወደብ ምዕራብ አቅጣጫ ከአንድ ሰዓት የጀልባ አሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውና ፍራሹ የሚታየው የአፄ ሱስንዮስ ቤተመንግሥት (ሱስንዮስ ግምብ) ሌላ መዳረሻ ሆኖ ይታያል፡፡ በሰሜናዊ ጣና ሐይቅ ዳርቻ የሚገኘው ጎርጎራና ዙሪያው በተፈጥሯዊና በሰው ሠራሽ በታሪካዊ ቅርሶች የበለፀገ መዳረሻ ነው፡፡
አፄ ሱስንዮስ ጎርጎራን ማዕከል ያደርጓት እንጂ ከሳቸው ንግሥና 300 ዓመታት በፊት ከነበሩት አፄ ዐምደ ጽዮን (1306 –1336 ዓ.ም.) ዘመን ጀምሮ በጎርጎራና አካባቢዋ፣ በጣና ሐይቅ ውስጥ በሚገኙት ደሴቶች በርካታ ገዳማት ተገንብተዋል፡፡ ቁጥራቸው 44 ስለደረሰም ‹‹አርባ አራቱ ጎርጎራ›› የሚልን ስያሜ ማትረፋቸውና ከአርባ አራቱ ጎንደር እንደሚቀድሙ ይወሳል፡፡
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ምዕራብ ደምቢያ ወረዳ የምትገኘው ጎርጎራ የጣና ሐይቅ ወደብ ከመሆኗ ባሻገር በደሴቶቿና በዳርቻዋ ስድስት ገዳማት (ደብረ ሲና ማርያም፣ ማን እንዳባ መድኃኔ ዓለም፣ ብርጊዳ ማርያም፣ ገሊላ ኢየሱስ፣ አንጋራ ተክለ ሃይማኖት፣ እጅ በራ ማርያም) አሏት፡፡ የአፄ ሱስንዮስ ቤተ መንግሥት ፍራሽ ቀልብን ከሚገዛ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ ጋር ሲታይ፣ የአካባቢው ደናማነት የብርቅዬ አዕዋፋት መናኸርያ አድርጎታል፡፡
የ700ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ
በጎርጎራ ከሚገኙት ጥንታዊና ታሪካዊ ገዳማት አንዷ የሆነችው ደብረ ሲና ማርያም ከተተከለች ኅዳር 21 ቀን 2012 ዓ.ም. 700 ዓመት ሞላት፡፡ የዘንድሮው ኅዳር ጽዮን በዓልም ከኢዮቤልዩ በዓሏ ጋር በመግጠሙ ከሩቅም ከቅርብም ከአገር ቤትም ከባሕር ማዶ ጭምር የተገኘው ምዕመንና ኅብረተሰብ ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡
የቱሪዝም መዳረሻዎችን ከማስተዋወቅና ከማስፋፋት ጋር በተያያዘ በርካታ ሥራዎችን እየሠራ የሚገኘው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ይህንን ታሪካዊ አጋጣሚ በዝምታ አላለፈውም፡፡ እጅግ አሳሳቢ በሆነውና በጎርጎራ ጣና ሐይቅ አካባቢ በሚገኙት ገዳማት ላይ የተፈጠረው የቅርስ አደጋ፣ ጎርጎራና አካባቢው ላይ ያለ የቱሪዝም አቅምና ያሉት ተግዳሮቶች እንዲሁም የደብረ ሲና ማርያም ገዳም ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ በዋዜማው ኅዳር 20 ቀን 2012 ዓ.ም. ሲምፖዚየም አካሂዷል፡፡
በመድረኩ እንደተወሳው፣ ገዳሟ ከሌሎች የሚለያት ባለሳር ክዳን መሆኗ ነው። የሯሷ መሬት ስለ ነበራት እስከ ዘመነ ደርግ አልተቸገረችም። በየዐረፍተ ዘመኑ ሳሩን ትለውጥ ነበር። መሬቷን ብመነጠቋ ሳር በማጠሩ አለማደሷ ያካባቢው ኅሰብ የሚሰጠው እንዳለ ሆኖ ዋጋ አስከፍሏታል። አራት ክፍለ ዘመን ያሳለፉ የግድግዳ ቅዱሳት ሥዕሎች፣ እየተበላሹ፣ እየተደመሰሱ ነው። ብራናዎችም እንዲሁ። ምስጥም ሌላው ፈተናዋ ነው። አስተማማኝ ጥበቃና ክብካቤ ባለመኖሩ ንዋየ ቅድሳት በተለያዩ ዘመናት ተዝርፈዋል።
የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን በ1978 ዓ.ም. እድሳት ከማድረጉ በቀር ለ30 ዓመታት አንዳች ነገር አለመፈጸሙ በቁጭት የተናገሩ አንድ አስተያየት ሰጪ እስከ መቼ ይላሉ።
ወ/ሮ ኂሩት እንዳመለከቱት፣ ሆኖም የገዳሟ የልማት ኮሚቴ ከማኅበረሰቡ ጋር በመተባበር በ1996 ዓ.ም. ሙሉ ጣራዋን ሳር አልብሰዋል። በ2005 ዓ.ም. ደግሞ ሳር የጎደለበትን አካባቢ ከመሙላት ባለፈ በተለይ በሚመለከተው የመንግሥት አካል የተደረገ እድሳት የለም። እንደ አጥኚዋ አገላለጽ፣ ገዳሟ በተለያየ ጊዜ መዘረፏ ሌላው ችግር ነበረ። ከቅርብ ጊዜ እንኳ በ1985 ዓ.ም. መጋቢት 23 ቀን የኪዳነ ምሕረት ጽላትና በርካታ ቅርስ ያጣችበት ሲሆን በ1997ም እንዲሁ ተዘርፋለች።
ከእነዚህ ጊዜያት በፊት ግን በርካታ የብራና መጻሕፍትን ጨምሮ ሌሎች ቅርሶችን እንዴት እንዳጣች አይታወቅም። በርካታ ቅርሶች አንደነበሩ ግን የዓይን እማኞች ይናገራሉ። አሁን ግን የግድግዳ ሥዕሎች ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑና ጥቂት የብራና መጻሕፍት ብቻ ይገኛሉ ብለዋል።
በመድረኩ የተገኘት የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አሥራት ዐፀደ ወይን (ዶ/ር) የደብረ ሲና ማርያም ገዳም የገጠማትን ፈተና በተለይም ጊዜ የማይስጡ ችግሮቿ ላይ ዩኒቨርሲቲያቸው ባለሙያዎች በመመደብ መፍትሔ ያበጃል ብለዋል። እንዲሁም በጎርጎራና አካባቢዋ የሚገኙ ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ ሀብቶችን ጠብቆ ለማልማት በጥናት የታገዘ ድጋፍ እንደሚደርግም ገልጸዋል።
እንደሳቸው አገላለጽ፣ ጎርጎራና አካባቢው በሰው ሠራሽና በተፈጥሮ ቅርሶች ቢበለጽግም በበቂ አልተዋወቀም። ማስተዋወቁ ባለመሠራቱ የሚጎበኙት የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ቱሪስቶች ቁጥር አነስተኛ ነው። አካባቢውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግም ከማስተዋወቁ በተጓዳኝ ሆቴሎችን፣ ሎጆችንና ሌሎች የአገልግሎት ሰጭ ተቋማት እንዲገነቡ ዩኒቨርሲቲው አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ተወስቷል።
የክልሉ የባህልና ቱሪዝም ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ መላኩ አላምረው፣ የቅርስ ጉዳይ እንደ አገር ሉዓላዊነት መታስብ እንደሚገባው በማስገንዘብ፣ ቅርስን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ማስተማር ማሳወቅ ይገባል ብለዋል። ቅርሶችን ለመጠበቅ የቱሪዝም ፖሊስ በተለይም የባሕር ላይ ፖሊስ ማሠልጠን አማራጭ እንደሌለውና ማኅበረሰቡም ተደራጅቶ መጠበቅም እንደሚገባው ጠቁመዋል። የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ለገዳሟ ዕድሳት ማስፈጸሚያ የገንዘብ ድጋፍ መላኩም በመድረኩ ተወስቷል።
“የጎርጎራ ችግር የሰው ማጣት ነው” በማለት በመድረኩ አስተያየት የሰጡት አዛውንት፣ በደርግ ዘመን የተከፈተው ወደብና ሆቴል እድሳትና ማስፋፊያ ሳይደረግለት እስካሁን መዝለቁ አካባቢው እንዳይለማ አድርጎታል፤“ ብለዋል።
ደብረ ሲና ማን ናት?
ደብረ ሲናን በ6812 ዓመተ ዓለም፣ በ1312 ዓመተ ምሕረት በጣና ሐይቅ ዳርቻ
የተከሏት ዐፄ ዓምደ ጽዮን ናቸው፡፡
“በጎርጎራ ከተማ ጣና ሀይቅ ዳርቻ የምትገኘውና፤ ሰፊ በማይባለው ግቢዋና አካባቢዋ በሚገኙት የእድሜ ባለጠጋ ረዣዥም ዛፎች ላይ፤ ጎጇቸውን በቀለሱት አዕዋፍት፤ በማዕልትም በሌሊትም ዝማሬ የሚሰማባት፤ የአካባቢዋን ተፈጥሯዊ ውበት፤ ከድንቅ ታሪኳ ጋር ይዛ፤ ዛሬም የምትመሰክረው ባለሳር ክዳኗ የደብረ ሲና ማርያም አንድነት ገዳም፤ ከአርባ አራቱ ጎርጎራ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ ናት፡፡” ይላል ለኢዮቤልዩ በዓሏ የታተመው መጽሔት።
መምህር ቆሞስ አባ ገብረ ሥላሴ ያሳይ፤ “የማን እንደ አባ ገዳምና አካባቢው ታሪክ“ በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ እንደገለጹት፣ ደብረ ሲና በምትሠራበት ጊዜም ታላቅ ተዓምር ተደርጓል። በዚያን ወቅት አብያተ ክርስቲያናት የሚሠሩት በአሥራ ሁለት ሰረገላ ወይም ወጋግራ ነበርና፤ ይህን ወጋግራ ለመግዛት ወደ ዘጌ/ዘንጌ/ ተብሎ ወደ ሚጠራው ቦታ ይሄዳሉ። እዛም የተፈለገውን ያህል ከዝግባ ዛፍ የተዘጋጀ ወጋግራ አገኙ፡፡ ሆኖም የነበራቸው ገንዘብ አሥራ አንዱን ብቻ የሚገዛ ነበር፡፡ አሥራ ሁለተኛውን ወጋግራ መግዛት ባለመቻላቸው እያዘኑ፤ የገዙትን ይዘው ተመለሱ፡፡ ደብረ ሲና ሲደርሱ ግን አሥራ ሁለተኛውን ወጋግራ ሐይቁ ዳር ተመለከቱት። እርስ በእርሳቸው ተያዩ፡፡ “ትተነው የመጣነው ወጋግራ አይደለንም“ ሲሉ ተጠያየቁ። ሲያስተውሉት ደግሞ እውነትም ያ ያልገዙት ወጋግራ እንደሆነ አወቁ፡፡
ወጋግራውን የገዙት ዘጌ ሐይቁ ዳርቻ ነበርና በእመቤታችን ተዓምር ወጋግራው ወደ ሐይቁ ገብቶ፣ በነፋስ እየተገፋ ወደ ደብረ ሲና ቀድሟቸው መጥቶ ሰላገኙት፤ ለሰው ልጆች አዛኝ የሆነችውን ድንግል ማርያምን አመሰገኗት፡፡ አሥራ ሁለቱን ዐምዶች ከቤተ ክርስቲያኑ በየቦታቸው አቆሟቸው፡፡ ይህ በተዓምር የመጣውን ወጋግራም በሴቶች መግቢያ በደቡብ ምዕራብ በኩል ተከሉት፡፡
የአፄ ሱስንዮስ ልጅ ማለትም የአፄ ፋሲል እህት እቴጌ መለኮታዊት፤ ወደ ደብረ ሲና መጥታ ከሐይቁ ተጠምቃ ከነበረባት ደዌ ትፈወሳለች፡፡ እቴጌዪቱ ከበሽታዋ ሰላዳነች፤ “ለደብረ ሲና ምን ላድርግ“ ብላ ከሊቃውንቱ ጋር ተማከረች፡፡ እነርሱም ቤተ ክርስቲያኗ የግድግዳ ሥዕል የላትምና አሠሪላት ይሏታል፡፡ እሷም በወቅቱ ጎጃም ውስጥ በሥዕል ችሎታቸው የሚታወቁ ወንድማማቾች ነበሩና፤ ተነጋግራ ሥዕሉን አሣለች፡፡ ሥነ ሥዕላቱ በዝናብ ፍሳሽ ምክንያት የተወሰነ ችግር ቢደርስባቸውም፤ ጥንታዊ ይዘቱን እንደጠበቀ ዘመናትን ተሻግሮ ዛሬ ላይ ደርሷል፡፡