የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ለብሔራዊ የኢኮኖሚ አማካሪ ምክር ቤት ገለልተኛ ዕጩ አባላት ለመቀበል፣ ማክሰኞ ታኅሳስ 21 ቀን 2011 ዓ.ም. ጥሪ አቀረበ፡፡ መንግሥት ገለልተኛ ብሔራዊ የአማካሪ ምክር ቤት ለማቋቋም መወሰኑን አስታውቋል፡፡
መንግሥት የኢኮኖሚ ሪፎርም ፕሮግራሙን በስኬት ለማስፈጸምና ጥራት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት ለማረጋገጥ፣ የምሁራንና የባለሙያዎችን ምክርና ግብረ መልስ መቀበል ጠቃሚ መሆኑን እንደሚያምን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታውቋል፡፡
በዚህም መሠረት ገለልተኛ ከሆኑ ምሁራንና ባለሙያዎች ሐሳብ መቀበል የፖሊሲ አካታችነትን እንደሚጨምር፣ የተለያዩ አመለካከቶች አገር ያለችበትን ውስብስብ የሆነ ድህነትና ተያያዥነት ያላቸው ማኅበረሰባዊ ችግሮችን ለመረዳትና ዘርፈ ብዙ የፖሊሲ አማራጮችን ለመመርመርና የመፍትሔ ሐሳቦችን ለማመንጨት እንደሚያስችሉ፣ እንዲሁም የመንግሥት ፖሊሲዎች በሕዝብና በተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት በኩል ያላቸውን ተቀባይነት እንዲጨምር ያግዛል ሲል ጽሕፈት ቤቱ ገልጿል፡፡
በመሆኑም መንግሥት ገለልተኛ የብሔራዊ የኢኮኖሚ አማካሪ ምክር ቤት ለማቋቋም መወሰኑን ጠቁሞ፣ ምክር ቤቱ ገለልተኝነቱን ጠብቆ በነፃነት እንደሚሠራና ከመንግሥት ጋር በየጊዜው እንደሚመክር አስረድቷል፡፡
የምክር ቤቱ አባላት ብዛት 15 እንደሚሆን እንደሚጠበቅ፣ በሙያቸው የተካኑና የተመሠገኑ፣ በዘርፉ የካበተ የሥራ ልምድ ያላቸው፣ የአገሪቱን የኢኮኖሚም ሆነ ማኅበረሰባዊ እውነታ ጠለቅ ብለው የተረዱ፣ የሐሳብ ልዩነትን በመረጃና በሐሳብ ውይይት በመፍታት የጋራ መፍትሔ የመሻት ክህሎት ያላቸውና ከሁሉም በላይ ለአገራቸውና ለሕዝብ ፍቅር ተቆርቋሪነት፣ እንዲሁም የአገልጋይነት መንፈስ የሚሰማቸው ሊሆኑ እንደሚገባ ጽሕፈት ቤቱ አመልክቷል፡፡
የብሔራዊ ኢኮኖሚ አማካሪ ምክር ቤቱን አባላት የመለየት ሒደት ግልጽና አሳታፊ እንዲሆን፣ መንግሥት በይፋ የዕጩ አባላትን ጥቆማ ለመቀበል መወሰኑን አስታውቋል፡፡ በመሆኑም ገለልተኛ የብሔራዊ ኢኮኖሚ አማካሪ ምክር ቤት አባል ሆኖ ለማገልገል ፍላጎት አለን ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ምሁራን፣ የግል ማኅደራቸውን ጥሪው ከቀረበበት ቀን ጀምሮ ባሉት ተከታታይ 15 ቀናት ውስጥ [email protected] በተባለው የኢሜይል አድራሻ እንዲልኩ አሳስቧል፡፡