ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለውሳኔ የቀረበው የኤክሳይዝ ታክስ ረቂቅ አዋጅ የሕዝቡን የመግዛት አቅም ያላገናዘበና የመንግሥትን ገቢም የሚጎዳ መሆኑን፣ የኢትዮ ተሽከርካሪዎች አስመጪ ባለቤቶች ማኅበር አስታወቀ፡፡ ረቂቅ አዋጁ የአገሪቱን ፖለቲካዊ ኢኮኖሚና የሰላም ሁኔታን ያላገናዘበ በመሆኑ መቅረት አለበት የሚል አቋም ይዟል፡፡
በኢትዮጵያ አስመጪዎች እንዲከፍሉ የሚጠየቀው የተሽከርካሪ ቀረጥ ከፍተኛ ሆኖ ሳለ በአንድ መኪና ላይ እስከ 500 በመቶ ድረስ ኤክሳይዝ ታክስ እንዲከፈል የሚጠይቀው ረቅቅ አዋጅ፣ የተጋነነ እንደሆነ ለሪፖርተር የገለጹት የማኅበሩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መሐመድ አመዴ ናቸው፡፡
‹‹ኤክሳይዝ ታክሱ የአንድን መኪና ዋጋ በአንዴ በብዙ እጥፍ የሚያንርና አስመጪዎችንም ሆነ የደንበኞችን አቅም ያላገናዘበ ስለሆነ፣ አስመጪዎች ማስመጣት እንዲያቆሙና መንግሥት ከጉምሩክ የሚያገኘው ገቢም በእጅጉ እንዲቀንስ የሚደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ባገለገሉ መኪኖች ላይ ይታሰብ የነበረው 33 በመቶ የእርጅና ቅናሽ መነሳቱ ዓለም አቀፍ አሠራርን የሳተ ‹‹ትልቅ ወንጀል›› ሆኖ ሳለ፣ ባገለገሉ ተሽከርካሪዎች ላይ እስከ 500 በመቶ ታክስ የሚጥለው ረቂቅ ሲዘጋጅ እንደ ባለድርሻ አካል ለውይይት ባለመጋበዛቸው አስቆጥቶናል የሚል መልዕክትም አስተላልፈዋል፡፡
በረቂቁ የተዘጋጀው ኤክሳይዝ ታክስ በየትኞቹ ተሽከርካሪዎች ላይ ተፈጻሚ ሊሆን ይገባል የሚለው በጥንቃቄ መታየት እንደሚገባው፣ አዲሱ ታክስ የነዳጅ ፍጆታና ጥራትን፣ እንዲሁም ተሽከርካሪዎቹ በሚሰጧቸው ጥቅሞች ታይቶ ሊጣል ይገባል ሲሉ አቶ አህመድ ተናግረዋል፡፡
ትልልቅ የነዳጅ ፍጆታ ያላቸው ተሽከርካሪዎች ከአየር ብክለት አኳያ፣ በነዳጅ ወጪም ረገድ ተለይተው ኤክሳይዝ ታክሱ ሊጣልባቸው እንደሚገባ፣ በሊትር እስከ 20 ኪሎ ሜትር በሚነዱት ላይ የተለየ አተያይ እንዲኖር ጠይቀዋል፡፡
ቀደም ሲል ኤክሳይዝ ታክስ የማይመለከታቸው የሕዝብ ማመላለሻ ሚኒባሶች፣ ዶልፊኖች፣ አባዱላዎች፣ ኮስተሮች፣ አይሱዙዎች፣ ፒክ አፖችና አውቶቢሶች በአዲሱ የኤክሳይዝ ታክስ መረብ ውስጥ እንዳይገቡም ጠይቀዋል፡፡ እነዚህ የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከኤክሳይዝ ታክስ ነፃ ከመሆን ባሻገር ወደ አገር ውስጥ ሲገቡ ይከፈልባቸው የነበረው ቀረጥም ከአሥር እስከ 30 በመቶ ነበር ብለዋል፡፡ ይህ ቀርቶ በረቂቁ ውስጥ የሚካተቱ ከሆነ ግን የትራንስፖርት ዋጋ በከፍተኛ መጠን እንዲጨምር ያደርጋል ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ተሽከርካሪዎች ጥንካሬ፣ የነዳጅ ፍጆታ፣ ከጋራዥ ባለሙያዎች ጋር ያላቸው ቁርኝት ታይቶ ‹‹የብራንድ መረጣ›› እንዲደረግም ሐሳብ አቅርበዋል፡፡
ረቂቁ አዋጁ የግድ ተግባራዊ መሆን ካለበትም ከመረቀቁ በፊት አገር ውስጥ በመግባት ሒደት ላይ የሚገኙ ተሽከርካሪዎች በነበረው የታክስ ሥርዓት እንዲታዩ ጠይቀዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ምን ያህል ተሽከርካሪዎች አገር ውስጥ በመግባት ሒደት ላይ እንደሚገኙ በውል ባይታወቅም 4,500 ያህል አስመጪዎች እንዳሉ፣ እያንዳንዳቸው በአንድ ጊዜ ከአሥር እስከ 120 መኪኖችን እንደሚያስገቡ፣ አንድ መኪና ግዥው ተጠናቆ አገር ውስጥ እስኪገባም ከሦስት እስከ አምስት ወራት እንደሚፈጅ በመግለጽ፣ የኤክሳይዝ ታክሱ ተፈጻሚነት ይህንን እንዲያገናዝብ ጠይቀዋል፡፡