አዲስ አበባ ቀደምት ከሚባሉ የኢትዮጵያ ከተሞች ተርታ ብትመደበም፣ መጠሪያዋን ስያሜው ያደረገ ብሔራዊ ስታዲየም ሳይኖራት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ዘመናዊ ስታዲየምም መመልከት ብርቅ ሆኖባት ዘመናት አልፈዋል፡፡ አንድ ለእናቱ የሆነው የአዲስ አበባ ስታዲየም የዓለም አቀፍ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) ለዚህ ወቅት የሚመጥን አይደለም በሚል ማንኛውንም አኅጉራዊም ይሁን ዓለም አቀፋዊ ውድድሮችን እንዳያስተናግድ ክልከላ ጥሎበታል፡፡
የማሻሻያ ሥራና ዕድሳት እየተደረገለት የሚገኘው የአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንደ ግንባታው ባጠናቀቅም፣ አሁን ላይ ግን ተስፋ ሰጪ መሆኑ እየተነገረለት ይገኛል፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ በአሁኑ ወቅት የግንባታው መጀመሪያ ምዕራፍ የተጠናቀቀው የአደይ አበባ ስታዲየም የቀደመውን የከተማዋን ገጽታ የሚቀይር መሆኑ እየታየ ነው፡፡
የግንባታውን መሠረት በ2008 ዓ.ም. ታህሣሥ ወር ላይ አንድ ብሎ የጀመረው የአደይ አበባ ስታዲየም፣ የመጀመሪያውን የግንባታ ምዕራፍ ለማጠናቀቅ አራት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ግንባታውን በባለቤትነት የሚመራው ስፖርት ኮሚሽን ታኅሣሥ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. የግንባታውን የመጀመሪያ ምዕራፍ መጠናቀቅ አስመልክቶ፣ ባለድርሻ አካላት ፕሮጀክቱን እንዲጎበኙት አድርጓል፡፡ የግንባታው የመጀመሪያው ምዕራፍ 98.8 በመቶ መጠናቀቁና እስካሁን 2.2 ቢሊዮን ብር ወጪ መደረጉን፣ የምዕራፍ ሁለት ግንባታውን ለማጠናቀቅ ደግሞ ሦስት ዓመታትን የሚጠይቅ መሆኑ ተገልጿል፡፡ ወጪውም ከመጀመሪያ ወጪ ጋር እንደሚቀራረብ ቅድመ ግምት አግኝቷል፡፡
ዓለም አቀፍ ደረጃውን ጠብቆ እየተገነባ የሚገኘው የአደይ አበባ ስታዲየም አራት ዋና ዋና በሮች ሲኖሩት፣ በወንበር 60,000 ተመልካቾችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል፡፡ ለክብር እንግዶች (ቪአይፒ) እና ለሚዲያ አባላት 2,000 ወንበሮችን የያዘ እንደሚሆንም የስፖርት ኮሚሽን የስፖርት ፋሲሊቲ ዳይሬክተር አዝመራው ግዛው (ኢንጅነር) አስረድተዋል፡፡
በኤም ኤች ኢንጂነሪንግ የግንባታው አማካሪ መሐንዲስና ተቆጣጣሪ መለሰ ለማ (ኢንጅነር) በበኩላቸው፣ ስታዲየሙ በየትኛውም ዓለም እንደሚገኝ ዘመናዊ ስታዲየም ደረጃውን ጠብቆ በጥንቃቄ እየተገነባ መሆኑን አውስተዋል፡፡ ግንባታው በቻይናው የግንባታ ተቋራጭ ቻይና ስቴት ኢንጂነሪንግ አማካይነት እየተከናወነ መሆኑም ታውቋል፡፡