“ጭቃ ማቡካትና ልጅነት የተሳሰሩ ናቸው፡፡ አንድ ሕፃን መዳህ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ጭቃ ሲያገኝ ያቦካል፣ በርሱም ይጫወታል፣ የራሱን ዕሳቤ በልዩ ልዩ ቅርፃ ቅርፅ እየፈጠረ ይመራመራል፡፡ መልሶ ደግሞ ያፈርሰዋል ደግሞ ያቦካዋል … ልጅነት እንዲህ እንዲህ እያለ ነው ያለፈው፡፡”
በቀደመው ጊዜ የነበረው ይህ የጭቃ ትውፊት፣ ከቅርብ ዘመናት ወዲህ በተለይ ከዋና ዋና ከተሞች እየራቀ የሄደበትን ገጽታ ዳግም ነፍስ ለመዝራት ያሰበው አንድ ተቋም፣ መጠርያውን ‹‹ኑ ጭቃ እናቡካ ፕሮሞሽን ኩባንያ›› አሰኝቶ እንቅስቃሴ ውስጥ ከገባ ሁለተኛ ዓመቱን ይዟል፡፡
ኩባንያው ‹‹ልጆቻችን በዛሬው ዘመን እየተጫወቱ ያሉት ራሳቸው ጭቃ አቡክተው በሠሩት ቅርፃ ቅርፅ ሳይሆን ሌሎች በፈበረኩላቸው የፕላስቲክ ቁሶች ሆኗል፡፡ ሌሎች ከእኛ ማንነት ባልተነሳ ዕሳቤ በቀየሱልን ቦይ እየፈሰስን እንገኛለን፡፡ የእኛን አስኳል ማንነታችንን ደግሞ መፈለግ የወቅቱ የህሊና ጥያቄ ነው፡፡ የኑ ጭቃ እናቡካ መነሻም ማንነትን ከመሠረታችን መልሶ መፈለግና ማደራጀት ነው፤›› በሚል መንደርደሪያ በመነሳትም በታላቁ ቤተ መንግሥት ውስጥ በሚገኘው አንድነት ፓርክ ጭቃን ማቡካት ማዕከሉን ያደረገ የልዩ ልዩ ዝግጅቶች መድበል ማዘጋጀቱን ገልጿል፡፡
ኩባንያው እንዳስታወቀው፣ ቅዳሜ ጥር 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ከ3፡00 እስከ 10፡00 ሰዓት በሚኖረው ዝግጅት የሸክላ ሥራ፣ ጥጥ መፍተል፣ መሸመን፣ ስፌት መስፋት፣ ሙልሙል መጋገር፣ ሥዕል መሣል፣ ፊት መቀባት፣ ከወዳደቁ ዕቃዎች መልሶ መጠቀም፣ ባህላዊ ውዝዋዜ፣ የልጅነት ጨዋታዎችና ሌሎች አዝናኝ ዝግጅቶች ይደረጋሉ::
የኑ ጭቃ እናቡካ! መርሐ ግብር በተለያዩ ክልሎች በመዘዋወር ልጆች በራሳቸው ማንነት አካባቢያቸውን በመቃኘት በተፈጥሮ እንዲጫወቱ ማድረግና ሐሳቡን በሕፃናቱ ልቦና ውስጥ የማስረፅ ሥራ እንደሚሠራም አስታውቋል፡፡
በ2011 ዓ.ም. ኑ ጭቃ እናቡካ ልዩ የቤተሰብ የደስታ ቀን በአዲስ አበባ ቦሌ 17/19 ፓርክ ሁለት ጊዜ ማድረጉን ኩባንያው አስታውሷል፡፡
ሕፃናትን ማዕከል ያደረገ ልጆች ባህላቸውንና ትውፊታቸውን አውቀው እንዲያድጉና ተተኪ እንዲሆኑ ለማድረግ የወጠነችው ሠዓሊት ሐመረ ሙሉጌታ ስትሆን፣ ይህንኑም በልጆቿ በመጀመር ከዚያም አካባቢዋ ባሉ ልጆች፣ በመቀጠልም በየትምህርት ቤቶችና በተለያዩ ዝግጅቶች ላለፉት ስድስት ዓመታት ሕፃናትንና ታዳጊዎችን በዕረፍት ቀናቸው የሚሰጡ በዓይነትና በይዘት የተለያዩ ትምህርቶችንና ክህሎቶችን ስታስተምር ቆይታለች፡፡