የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለተመዘገቡ የአገር አቀፍና የክልል ፓርቲዎች በአዋጅ ቁጥር 1162/2011 መሠረት ማሟላት ያሉባቸው ግዴታዎች መመርያ አፀደቀ፡፡ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአዋጁ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባን አስመልክቶ፣ ታኅሳስ 26 ቀን 2012 ዓ.ም. መመርያ ማፅደቁን አስታውሷል፡፡
የአዋጁን ድንጋጌ ለማስፈጸም የወጣው የአሁኑ መመርያ ከመፅደቁ በፊት ከፓርቲዎች ጋር የተለያዩ ውይይቶች መደረጋቸውን፣ ሰባት ፓርቲዎች ደግሞ በጽሑፍ ለቦርዱ ግብዓት ማስገባታቸውን ባወጣው መግለጫ ገልጿል፡፡
በመመርያው የተካተቱ ዋና ዋና ጉዳዮችም ሁሉም ተመዝግበው የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአዋጁ የተቀመጠውን የመሥራች አባላት ፊርማ ለማሟላት ሁለት ወራት የጊዜ ገደብ እንዳላቸው፣ ጠቅላላ ጉባዔ ሳያካሂዱ ጊዜ ያለፈባቸው ፓርቲዎች በአዋጁ መሠረት አሟልተው በሁለት ወር ውስጥ ማሳወቅ እንደሚጠበቅባቸው፣ ጠቅላላ ጉባዔ በወቅቱ ያካሄዱ አገር አቀፍ ፓርቲዎች በአዲሱ አዋጅ ላይ የተቀመጠውን የጠቅላላ ጉባዔ መሥፈርት በማሟላት እስከ ጥር 2012 ዓ.ም. ድረስ አጠናቀው ማቅረብ ይኖርባቸዋል ሲል ቦርዱ አስረድቷል፡፡
በተጨማሪም ጠቅላላ ጉባዔ በወቅቱ ያካሄዱ ክልላዊ ፓርቲዎች በአዲሱ አዋጅ የተቀመጠውን የጠቅላላ ጉባዔ መሥፈርት ለማሟላት እስከ ታኅሳስ 2012 ዓ.ም. ድረስ አጠናቀው ማቅረብ እንደሚኖርባቸው፣ በቦርዱ ያልተመዘገቡ ነገር ግን በቀድሞው ሕግ በሒደት ላይ ያሉ በቀድሞው መሟላት ያለበትን አጠናቀው በአዲሱ አዋጅ ያሉትን መሥፈርቶችም ጨምረው በጋራ ማጠናቀቅ እንደሚጠበቅባቸው፣ እንዲሁም አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ብሔረሰቦችን የሚወክሉ ፓርቲዎች ሕጉ ላይ ያለውን የመሥራች አባላት ቁጥር ከማሟላት መሥፈርት ነፃ መሆናቸውን ቦርዱ አስታውቋል፡፡
ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሁሉም የተመዘገቡና በሒደት ላይ ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ማሟላት የሚገባቸውን መሥፈርትና የጊዜ ገደብ የሚገልጽ ደብዳቤ በሚቀጥሉት ጥቂት ቀናት ውስጥ ለሁሉም ፓርቲዎች እንደሚያደርስ ጠቁሟል፡፡
ፓርቲዎች ማሟላት ያሉባቸው መሥፈርቶች ላይ ከመሥራች አባላት ጋር የተገናኙት (አሥር ሺሕና አራት ሺሕ) ከምርጫው በፊት መሟላት ያለባቸው መሆኑን፣ ከጠቅላላ ጉባዔ ጋር የተገናኙት ግን ከምርጫ በኃላ በ2013 ዓ.ም. የሚያሟሉት እንደሚሆን፣ ይህም የተደረገው በቀድሞው ሕግ መሠረት ጠቅላላ ጉባዔያቸው በትክክል የተከናወነ ፓርቲዎችን ከምርጫ ሥራ ጋር ተደርቦ ጫና እንዳይኖርባቸው ታስቦ መሆኑን ቦርዱ ገልጿል።