በአማራ ክልል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ክስ በተመሠረተባቸው በእነ አቶ በረከት ስምዖን የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንንና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ገዱ አንዳርጋቸውን በመከላከያ ምስክርነት ቆጠሩ፡፡
ከጥረት ኮርፖሬት ኩባንያዎች ጋር በተያያዘ የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል በማለት የክልሉ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ ክስ የመሠረተባቸው አቶ በረከት ስምዖን፣ አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) እና አቶ ዳንኤል ግዛው (የዲቬንቱ ኩባንያ ባለድርሻ) የተመሠረተባቸውን ክስ እንዲከላከሉ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
በመሆኑም ተከሳሾቹ ከላይ የተጠቀሱት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት የተከሰሱበት ጉዳይ በመከላከያ ምስክርነት ቀርበው ለፍርድ ቤቱ የምስክርት ቃላቸውን እንዲሰጡላቸው መጥሪያ ማድረሳቸውን፣ ሐሙስ ታኅሳስ 30 ቀን 2012 ዓ.ም. ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ነገር ግን በመከላከያ ምስክርነት የተቆጠሩት ባለሥልጣናት፣ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡ ምስክሮቹ ባለመቅረባቸው በትክክል መጥሪያ ስለመድረሱ ፍርድ ቤቱ ሲጠይቅ፣ ተከሳሾች መጥሪያውን ማድረሳቸውንና ለጸሐፊዎቻቸው አስፈርመው መስጠታቸውን አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ለተከሳሾች እንዳስረዳው ባለሥልጣናቱ በምስክርነት የተቆጠሩት ባላቸው ሥልጣንና የሥራ ሁኔታ ሳይሆን በግል ደረጃ በመሆኑ፣ መጥሪያው ሊደርሳቸው የሚገባው በእጃቸው ስለሆነ ‹‹ደርሷል›› የተባለው መጥሪያ ላይደርሳቸው እንደሚችል አስረድቷል፡፡ በመሆኑም በድጋሚ መጥሪያ ወጪ ተደርጎ እንዲደርሳቸው በማለት ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ሌሎች ምስክሮች ማለትም አቶ በረከትና አቶ ታደሰ የቆጠሯቸው መከላከያ ምስክሮች ሳይሰሙ ቀርተዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ እነ አቶ በረከት በመከላከያ ማስረጃነት ያቀረቡት የሰነድ ማስረጃን ዓቃቤ ሕግ ከጽሕፈት ቤት ማግኘት አለመቻሉንና በዕለቱ ከፍርድ ቤት የተረከበ መሆኑን ገልጾ፣ ስላላየው የመዘጋጃ ጊዜ እንዲሰጠው በመጠየቁ ነው፡፡
የሦስተኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል የመከላከያ ምስክሮችን በሚመለከት ዓቃቤ ሕግ ችግር እንደሌለበት ለፍርድ ቤቱ በመግለጹ፣ ታኅሳስ 30 እና ጥር 1 ቀን 2012 ዓ.ም. ተሰምተው ተጠናቀዋል፡፡ የባለሥልጣናቱ መጥሪያ ደርሶ የመከላከያ ምስክርነቱን ለመስማት ለሰኞ ጥር 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡