የአዲስ አበባ ከተማ ባለአደራ ምክር ቤት (ባልደራስ) መሥራች አቶ እስክንድር ነጋና ባልደረቦቹ፣ የፖለቲካ ፓርቲ እየመሠረቱ መሆኑን አስታወቁ፡፡ የፓርቲውን ቅድመ ምሥረታ ስብሰባም እሑድ ጥር 3 ቀን 2012 ዓ.ም. እንደሚያደርጉም ተናግረዋል፡፡
አቶ እስክንድር ለሪፖርተር፣ ‹‹ፓርቲ ለመመሥረት ቅድመ ዝግጀት አድርገናል፡፡ የቅድመ ምሥረታ ስብሰባችን ጥር 3 ቀን 2012 ዓ.ም. በኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል እናደርጋለን፤›› ብሏል፡፡
ከምሥረታው አስተባባሪዎች አንዱ የሆነው አቶ ስንታየሁ ቸኮልም እንዳስረዳው፣ የምርጫና የፖለቲካ ፓርቲዎች አዋጅ ቁጥር 1162/2011 በሚደነግገው መሠረት ለምሥረታ ማሟላት ያለባቸውን የ200 አባላት ፊርማ አሟልተዋል፡፡
ጥር 3 ቀን 2012 ዓ.ም. በኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል በሚያደርጉት ስብሰባ ሊቀመንበርና የምክር ቤት አባላት ምርጫ ያደርጋሉ፡፡ በስብሰባውም የፓርቲው ስያሜ ‹‹ባልደራስ›› ወይም ሌላ ስለመሆኑ ተወያይተው በመሰየም፣ በቀናት ውስጥ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንደሚያሳውቁ ተናግረዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ በአዋጁ መሠረት ቅድመ ዕውቅና በሳምንት ጊዜ ውስጥ እንደሚሰጣቸው፣ በሦስት ወራት ውስጥ አስፈላጊውን ሁሉ በማሟላት ጠቅላላ ጉባዔ በማድረግ፣ ሙሉ ዕውቅና እንደሚያገኙ ተናግረዋል፡፡ የሚመሠርቱትን የፖለቲካ ፓርቲ ስያሜ ለማወቅ ሪፖርተር ጥረት ቢያደርግም፣ ከስብሰባው በፊት መግለጽ እንደማይቻል በመግለጻቸው አልተሳካም፡፡
የባለአደራው ሰብሳቢ አቶ እስክንድር ከሦስት ሳምንታት በፊት በአሜሪካ ቆይታ ካደረገ በኋላ፣ ዓርብ ጥር 1 ቀን 2012 ዓ.ም. ወደ ኢትዮጵያ ተመልሷል፡፡