[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚስታቸው ጋር ቁርስ እየበሉ ነው]
- ብላ እንጂ?
- በቃኝ እባክሽ፡፡
- መቼ በላኸው?
- ዘግቶኛል፡፡
- አልጣፈጠህም እንዴ?
- እሱስ አሪፍ ነበር፡፡
- ታዲያ ለምን አትበላም?
- አልወርድልህ አለኝ፡፡
- ምን ሆነሃል?
- ምን አልሆንኩም ብለሽ ነው?
- ምነው?
- የአገራችን ጉዳይ ነዋ፡፡
- የሚያሳስብ ነገር ተፈጠረ እንዴ?
- አገራችን አሳሳቢ ከሆነች እኮ ሰነባበተች፡፡
- አንተ ደግሞ የማያስጨንቅ ነገር ያስጨንቅሃል፡፡
- እንዴት?
- አሁን ስንት የሚያስጨንቅ ነገር እያለ ስለአገር ትጨነቃለህ?
- ከአገር በላይ ምን የሚያስጨንቅ ነገር አለ?
- ስለራስህ ነዋ መጨነቅ ያለብህ፡፡
- እ…
- ተመልከተን እስቲ?
- ማንን ነው የምመለከተው?
- እኛን ነዋ፡፡
- ምን ሆንን?
- አንተ ምን አለብህ?
- እንዴት?
- እኔ እኮ ሁሉንም ነገር ሳጣራ ነበር፡፡
- ምንድነው የምታጣሪው?
- ስለበፊቶቹ ባለሥልጣናት ሕይወት ነዋ፡፡
- ማለት?
- ለምሳሌ በጥምቀት የሚያደርጉትን ልንገርህ፡፡
- ምን ያደርጋሉ?
- እንደ ጥምቀት የሚወዱት በዓል አልነበረም አሉ፡፡
- ለምን?
- ብዙ ነገር የሚወራወሩበት በዓል ነዋ፡፡
- አልገባኝም?
- መቼም በጥምቀት ሎሚ እንደሚወረወር ታውቃለህ?
- እንዴት ማለት?
- በቃ ከባለሀብቶች ጋር የሚተጫጩበት በዓል ነው፡፡
- እ…
- አያንዳንዱ ባለሀብት መኪና ይወረውራል አሉ፡፡
- ለማን?
- ለክቡር ሚኒስትሩ ነዋ፡፡
- እሺ፡፡
- ሌላው ደግሞ ቪላ አሉ፡፡
- እ…
- ሙሉ የቤት ዕቃ የሚወረውርም አለ አሉ፡፡
- ወይ ጣጣ፡፡
- እሱ ብቻ መሰለህ እንዴ?
- ሌላ ደግሞ ምን አለ?
- የባንክ ሼር በለው ኧረ ስንቱን ልጥራው?
- እ…
- ባለሥልጣናቱም ግን በተራቸው ይወረውራሉ፡፡
- ምንድነው የሚወረውሩት?
- መሬት!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከተቃዋሚ መሪ ጋር ተገናኝተው እያወሩ ነው]
- ምንድነው ክቡር ሚኒስትር?
- ምኑ?
- አገሪቱ ወዴት እያመራች ነው?
- ወደ ብልፅግና ነዋ፡፡
- ፅድቁ ቀርቶብኝ በቅጡ በኮነነኝ አሉ፡፡
- ተረት ትችላለህ እንዴ?
- ምን ለማለት ፈልገው ነው?
- ማለቴ ያው ዳያስፖራ ነህ ብዬ ነው፡፡
- ወድጄ አይደለም እኮ ዳያስፖራ የሆንኩት፡፡
- ደግሞ ማን አስገደደህ?
- አላታግል ሲሉኝ እኮ ነው ከአገር የሸሸሁት፡፡
- ታዲያ ምን አጠፉ?
- ምን አሉኝ?
- ምንም፡፡
- ልታባርሩን አስባችኋል እንዴ?
- መቼ ይቀራል?
- እ…
- ምነው?
- እኛ እኮ መንግሥትን አምነን ነው የመጣነው፡፡
- መንግሥትም አምኖ ነበር የጠራችሁ፡፡
- ምን አምኖ?
- አገሪቱ ሰላም ትሆናለች ብሎ ነዋ፡፡
- እ…
- አተርፍ ባይ አጉዳይ አሉ፡፡
- ማን ነው እሱ?
- መንግሥት ነዋ፡፡
- እንዴት?
- ይኸው የአገሪቱ ሰላም በየጊዜ እየደፈረሰ ነዋ፡፡
- እኛ እጃችን የለበትም፡፡
- እሱን ስትጠየቅ ታወራለህ፡፡
- ማን ነው የሚጠይቀኝ?
- ምን አስቸኮለህ?
- እያስፈራሩኝ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ዓላማህ ለመሆኑ ምንድነው?
- ሕዝቤን ማገልገል ነዋ፡፡
- ማጋደል ነው ያልከኝ?
- ተው እንጂ ክቡር ሚኒስትር?
- ትንሽ ግን አያሳዝናችሁም፡፡
- ማን ነው የሚያሳዝነን?
- ሕዝቡ ነዋ፡፡
- ትግል፣ ትግል ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ይኼ ሕዝብ መቼ ይሆን የሚያልፍለት?
- አሁን በእኛ ያልፍለታል፡፡
- በእናንተማ ሕይወቱ እያለፈ ነው፡፡
- ምን አሉኝ?
- ለማንኛውም ደርሰንበታል፡፡
- ምኑን?
- ዓላማህን፡፡
- ምንድነው?
- ማተራመስ!
[ለክቡር ሚኒስትሩ የቀድሞ ሚኒስትር ስልክ ደወሉላቸው]
- ምን አለ ብታምኑ ክቡር ሚኒስትር?
- ምኑን?
- ሁሉም ነገር እያፈሰሰባችሁ እኮ ነው፡፡
- አልገባኝም?
- ፖለቲካውን ስትሉት ኢኮኖሚው እያለ አስቸገራችኋ?
- እ…
- ለምን አትለቁልንም?
- ለእናንተ?
- የውጭዎቹም መቼ ቻሉት?
- ምን?
- የእነሱን ምክር መስማት እንደማያዋጣ ተናግረን ነበር፡፡
- የምነግርህ ነገር የእነሱ ምክር ቢያንስ ከእናንተ ይሻላል፡፡
- ክቡር ሚኒስትር የሁሉም ነገር መፍቻ በእጃችን ነው፡፡
- እናንተ ማጥፊያ እንጂ መፍቻ የላችሁም፡፡
- እ…
- ተስፋ እንዴት አትቆርጡም?
- እኛማ መመለሻ ትኬታችንን ነው መቁረጥ የምንፈልገው፡፡
- የት ነው የምትመለሱት?
- አራት ኪሎ፡፡
- ወደዚህ ከተመለሳችሁም የምትመለሱት አንድ ቦታ ነው፡፡
- የት?
- ቂሊንጦ፡፡
- እንግዲያው እንቀጥላለን፡፡
- ምኑን?
- ትግላችንን ነዋ፡፡
- ትግል እኮ ድሮ ቀረ፡፡
- እንዴት?
- በዚህ ዘመን ምርጫ ነው ያለው፡፡
- እ…
- እናንተ ደግሞ ተመራጭ አለመሆናችሁን መቼም ታውቁታላችሁ?
- ክቡር ሚኒስትር እኛ ተመራጭም ተደማጭም ነን፡፡
- ደፍጣጭ ነን ብትል ነው የሚያምርብህ፡፡
- ሥልጣን የያዝነው በምርጫ መስሎኝ?
- እኔ ለዚህ አይደል እንዴ ደፍጣጮች ናችሁ የምልህ?
- ክቡር ሚኒስትር እርስዎንም ለዚህ ያበቃንዎት እኛ መሆናችንን አይርሱት፡፡
- ወዳችሁ ሳይሆን ተገዳችሁ ነው እባክህ?
- እ…
- ለማንኛውም አደብ ብትገዙ ይሻላችኋል፡፡
- እናንተም አገሩን በሥርዓቱ ብታስተዳድሩት ይሻላችኋል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እናንተ እያላችሁ እንዴት አድርገን?
- ታዲያ አንድ ላይ እናስተዳድረዋ?
- እሱ የማይታሰብ ነው፡፡
- በቃ?
- አዎ በቃ፡፡
- እንግዲያው ተከታታይ ድግሶች አዘጋጅተንላችኋል፡፡
- የምን ድግስ?
- የብጥብጥ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ለአንድ ባለሀብት ስልክ ደወሉ]
- እንኳን አደረሰዎት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ለምኑ?
- ለጥምቀት ነዋ፡፡
- በደረቁ ምን ያደርጋል ብለህ ነው?
- በምን ላርጥብልዎት ክቡር ሚኒስትር?
- ለበፊቶቹ ሚኒስትሮች በምን ነበር የምታረጥብላቸው?
- እ…
- የማላውቅ መሰለህ እንዴ?
- ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
- ለበፊቶቹ ምን ታደርግ እንደነበር ነዋ፡፡
- ምን እያሉኝ ነው?
- አሁን ምነው በደረቁ እያልኩህ ነዋ፡፡
- አልታወቀም ብዬ ነው፡፡
- ምኑ?
- መቀመጫችሁ ነዋ፡፡
- ከአሁን በኋላ ማን ይነቀንቀናል?
- ክቡር ሚኒስትር ከየአቅጣጫው እየተወዘወዛችሁ እኮ ነው፡፡
- እ…
- ባይሆን ቀልጣፋ ከሆኑ ያቀላጥፉኝ፡፡
- ምን?
- አንድ አሪፍ ፕሮጀክት ነበረኝ፡፡
- ታዲያ ምን ገጠመህ?
- ፕሮጀክቱን ለመተግበር ዋነኛ እንቅፋት የሆነብኝ ነገር አለ፡፡
- ምንድነው?
- መሬት፡፡
- እ…
- በቃ እሱን ከቀረፉልኝ የፈለጉትን ነገር እወረውርልዎታለሁ፡፡
- እውነት?
- ምን ጥያቄ አለው፡፡
- እንግዲያው ወርውርልኝ፡፡
- ምን?
- ቪላ!