የታገቱት የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ፣ መንግሥት ግልጽ መረጃ እንዲሰጥ የአማራ ክልል ነዋሪዎች ሰላማዊ ሠልፍ በማድረግ ጠየቁ፡፡
በአማራ ክልል በጎንደር፣ በደሴ፣ በደብረ ማርቆስ፣ በዳንግላ፣ በወልዲያ፣ በደብረ ብርሃን፣ በባህር ዳርና በሌሎች በርካታ ከተሞች ማክሰኞ ጥር 19 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረጉት አጋቾችን የማውገዝ ሰላማዊ ሠልፍ ላይ ነዋሪዎች እንደተናገሩት፣ በደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ይማሩ የነበሩ 13 ሴትና አራት ወንድ ተማሪዎች በማንና እንዴት እንደታገቱ ሳይገለጽ ሁለት ወራት ሊሞላቸው ነው፡፡ ተማሪዎቹ የወላጆቻቸው ብቻ ሳይሆኑ የመላው ኢትዮጵያውያን ልጆች መሆናቸውን፣ መንግሥት ስለሚገኙበት ሁኔታ ግልጽ መረጃ ሊሰጥ እንደሚገባ፣ እንዲሁም በአጋቾች ላይም ዕርምጃ በመውሰድ የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ አለበት ብለዋል፡፡
መንግሥት ይህንን ያህል ቀናት ዝምታን የመረጠው የታገቱት ተማሪዎችን ከእነ ሙሉ ጤንነታቸውና ደኅንነታቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ እያመቻቸ ነው የሚል እምነት እንደነበራቸው የገለጹት ሠልፈኞቹ፣ ነገር ግን ከበቂ በላይ ቀናት ስላለፉ ሳይውል ሳያድር ወደ ቤተሰቦቻቸው በሰላም እንዲመለሱ እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡ በሌሎች አገሮች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ ‹‹ተማሪዎቻችንን መልሱ፣ ዝምታው ይሰበር›› እያሉ በተለያዩ መገናኛ ዘዴዎች ጥያቄዎቻቸውን እያቀረቡና ድርጊቱን እያወገዙ በሚገኙበት ወቅት፣ መንግሥት ለምን ዝምታ እንደመረጠም እንዲያሳውቅ ጠይቀዋል፡፡ በአንዳንድ ሠልፎች ላይም በከፍተኛ ተቃውሞ የታጀቡ መፈክሮችን የያዙ ሲታዩ፣ ስድብና ዘለፋም ያነገቡ ተስተውለዋል፡፡
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በበኩሉ ባወጣው መግለጫ በተለያዩ የአማራ ክልል ከተሞች ሰላማዊ ሠልፍ በማድረግ ሠልፈኞቹ ያቀረቡትን ጥያቄ፣ መንግሥት ሳይውል ሳያድር እንዲመልስ ጠይቋል፡፡ በየመገናኛ ብዙኃኑ ብቅ እያሉ በታገቱት ተማሪዎች ላይ የሚሳለቁ ባለሥልጣናት ለሕግ እንዲያቀርብ ጥያቄውን አቅርቧል፡፡
ተማሪዎቹ መታገታቸው ከተሰማ ሁለት ወራት ሊሞላቸው ሲሆን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ አቶ ንጉሡ ጥላሁን በሰጡት መግለጫ 21 ተማሪዎችን በድርድር ማስለቀቅ መቻሉንና ስድስት ተማሪዎች ግን እንደቀሩ መግለጻቸው ቢታወስም፣ ተማሪዎቹ እስካሁን ከቤተሰቦቻቸው ጋር አለመገናኘታቸውና የት እንዳሉም አለመታወቁ እየተገለጸ ነው፡፡
ሰሞኑን ደግሞ በሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል የሚመራ ልዑክ ወደ ሥፍራው በማቅናት ውይይት ላይ መሆኑ ተሰምቷል፡፡ በዚህ የጭንቀት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ዝም በማለታቸው ደግሞ ብዙዎች ግራ መጋባታቸውን እየገለጹ ነው፡፡