የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በሥሩ የሚገኘው የድንገተኛ አደጋዎች ምላሽ ማስተባበሪያ ማዕከል፣ በኮሮና ቫይረስ ተጠርጥረው በጥቆማ የቀረቡለት 29 ሰዎች ላይ ማጣራት ማድረጉን አስታወቀ፡፡
ኢንስቲትዩቱ ኮሮና ቫይረስን አስመልክቶ ዓርብ ጥር 29 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የቫይረሱን ሥርጭት አስመልክቶ 29 ጥቆማዎች ለማዕከሉ (Emergency Operation Center) ደርሰዋል፡፡
በ29 ተጠርጣሪዎች ላይ በተደረገው ማጣራት 14 ያህሉ በቫይረሱ የመያዝ ምልክት ያሳዩ ስለነበረ ተለይተው ወደ መቆያ ሥፍራ (Isolation center)) እንዲገቡ መደረጋቸውን፣ ወደ ደቡብ አፍሪካ 11 ናሙናዎች ተልከው ስምንቱ ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸው መረጋገጡን፣ ሦስት ናሙናዎች ወደ ደቡብ አፍሪካ ተልከው የምርምራው ውጤት እየተጠበቀ እንደሆነና በቀጣዮቹ ቀናት ቀሪዎቹ ናሙናዎች ለምርመራ እንደሚላኩ አስታውቋል፡፡
የኮሮና ቫይረስ መነሻ ከሆነችው ከቻይና ውሃን ከተማ የሚመጡ ማናቸውም መንገደኞች ወደ ለይቶ ማቆያ ማዕከል እንዲገቡ ተወስኗል ያለው ኢንስቲትዩቱ፣ በመሆኑም ወደ አገር ውስጥ እንደገቡ በተዘጋጀው ለይቶ ማቆያ ውስጥ ሆነው አስፈላጊው የሕክምና ክትትል የሚደረግላቸው መሆኑን ገልጿል፡፡
በቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ከቻይና የሚመጡ መንገደኞች ከሌሎች መንገደኞች ጋር ሳይቀላቀሉ የሙቀት ምርመራ የሚደረግላቸው መሆኑን፣ እንዲሁም ከቻይና ለሚመጡ መንገደኞች ብቻ አገልግሎት የሚሰጥ የኢሚግሬሽን ልዩ መስኮት እንደተዘጋጀላቸው ተጠቁሟል፡፡
ከቻይና የሚመጡ መንገደኞችን የጤና ሁኔታ መከታተል እንዲቻል ለባለሙያዎች ሥልጠና ተሰጥቶ አገልግሎቱም መጀመሩን፣ በቦሌ ኤርፖርት ለሚሠሩ ሁሉም አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ እየተሰጠ መሆኑን ከኢንስቲትዩቱ መግለጫ ለመረዳት ተችሏል፡፡
በዓለም የጤና ድርጅት ሪፖርት መሠረት እስከ ዓርብ ጥር 29 ቀን 2012 ዓ.ም. አመሻሽ ድረስ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች ቁጥር ከ31 ሺሕ በላይ ሲሆን፣ 635 ሰዎች በቫይረሱ ምክንያት ሕይወታቸው ማለፉ ተረጋግጧል፡፡ በ24 ሰዓት ውስጥም 69 ሰዎች መሞታቸው ሪፖርት ተደርጓል፡፡