[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ዳያስፖራ ስልክ ደወለላቸው]
- እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
- ሰላም ወዳጄ፡፡
- ምን ሆነው ነው ስልክ የማያነሱት?
- የእኛን ነገር እያወቅከው፡፡
- ምኑን?
- ቢዚ መሆናችንን ነዋ፡፡
- አይ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምነው?
- ሕዝቡ የሚፈልገው እኮ ቢዚ መሆናችሁን አይደለም፡፡
- ታዲያ ሌላ ምን ይፈልጋል?
- ጥቅሙን ማስከበራችሁን ነዋ፡፡
- ለዚያ አይደል እንዴ ቢዚ የሆነው፡፡
- አልመሰለኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን እያልክ ነው?
- ሕዝቡ ምን እያለ እንደሆነ አልሰሙም?
- ስለምኑ?
- ስለግድቡ ነዋ፡፡
- ምን አለ ደግሞ?
- ክቡር ሚኒስትር ሁላችንም ሥጋት ውስጥ ነን፡፡
- ለምን?
- የለፋንበት ግድብ መና እንዳይቀር ሠግተን ነዋ፡፡
- እንዴት ሆኖ?
- ድርድሩ ግብፅን እንጂ ኢትዮጵያን የሚጠቅም አይደለም፡፡
- ማን ነው ያለው?
- ሚዲያው ሁሉ እሱን አይደል እንዴ የሚያወራው?
- ወሬኞች በላቸው፡፡
- እነሱ ምን አደረጉ?
- ይኸው እነሱ አሉባልታቸውን እየረጩ ሥራ መሥራት አቃተን፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እነሱም እኮ ሥራቸውን እየሠሩ ነው፡፡
- አሉባልታ ማሠራጨት ነው ሥራቸው?
- እናንተ ወጥታችሁ በግልጽ ካላወራችሁ አሉባልታ መወራቱማ አይቀርም፡፡
- እኛ እኮ አገራችንን እንወዳለን፡፡
- ታዲያ በሥራ አሳዩና?
- ምን እያልክ ነው?
- ይኸው እናንተ አገሪቱን እየመራችኋት አይደል እንዴ ቀውስ በቀውስ የሆነችው?
- እኛ ምን አደረግን?
- ክቡር ሚኒስትር ጣት መጠቋቆሙ አያዋጣችሁም፡፡
- ማን ጠቆመ?
- ይኸው እኛ ምን አደረግን ምናምን እያሉ አይደል እንዴ?
- እ…
- ብቻ ለማንኛውም ሁላችንም እየተከታተልናችሁ ነው፡፡
- በምኑ?
- በህዳሴ ግድቡ ጉዳይ ነዋ፡፡
- እንግዲህ የቻልነውን እናደርጋለን፡፡
- ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአገሩ ቀልድ እንደማያውቅ ያውቃሉ፡፡
- እሱማ ግልጽ ነው፡፡
- እንግዲያው አንድ ነገር ልንገርዎት?
- ምን?
- በግድቡ የሚነሳ ቁጣ…
- እ…
- አይገደብም!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከሌላ ሚኒስትር ጋር ተገናኝተው እያወሩ ነው]
- ምንም አላማረኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምኑ?
- አካሄዳችን ነዋ፡፡
- ምን እያልክ ነው?
- ሕዝቡ ደስተኛ አይደለም፡፡
- በምኑ?
- በብዙ ነገሮች፡፡
- ምን እናድርግ ታዲያ?
- መነጋገር አለብን፡፡
- አንድ ላይ አይደል እንዴ አገር እየመራን ያለነው?
- ነበር ባይሰበር፡፡
- አልገባኝም ምን እያልክ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ሁሉም እንዳሻው ነው እየተጓዘ ያለው፡፡
- ማለት?
- በአገራችን ጉዳይ ሌሎች ገብተው እየፈተፈቱ አይደል እንዴ?
- ምን አልከኝ?
- ክቡር ሚኒስትር አገራችን በሯ ተበረጋግዷል፡፡
- እ…
- ይህ ደግሞ ለብዙ ችግሮች ሊዳርገን ይችላል፡፡
- የምታወራው ምንም አልገባኝም?
- እንዲገባዎት ካልፈለጉማ እንዴት ይገባዎታል?
- አስረዳኝ እያልኩህ እኮ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ሁሉም በየፊናው የፈለገውን እያደረገ ነው እኮ፡፡
- ለምን በግልጽ አትነግረኝም?
- አገሪቱ በጎረቤት አገሮች ሰላዮች ተሞልታለች፡፡
- እ…
- የቀድሞ ጓዶቻችንን ለማናደድ ብለን እየሄድንበት ያለው ርቀት አደገኛ ነው፡፡
- እ…
- በዚያ ላይ በተለያዩ ቦታዎች ለሚፈጠሩ ግጭቶች አንዳንድ ባለሥልጣናት እጃቸው እንዳለበት መረጃዎችም አሉን፡፡
- ይኼማ ሊሆን አይገባም፡፡
- በሚያሳዝን ሁኔታ ግን እየሆነ ነው፡፡
- እ…
- በተለይ ከሌሎች አገሮች ጋር ያለን ግንኙነት በመርህ ላይ የተመሠረተ ሊሆን ይገባዋል፡፡
- ትክክለኛ ነጥብ ነው ያነሳኸው፡፡
- እየተደረገ ያለው ግን ሌላ ነው፡፡
- እ…
- ለማንኛውም ሕዝቡም እየታዘበን ነው፡፡
- እኛን?
- ምን ጥያቄ አለው፡፡
- ወይ ጣጣ፡፡
- ከዚያም አልፎ መልዕክት እያስተላለፈ ነው፡፡
- ምን ብሎ?
- አታሽቃብጡ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ጋር ተገናኙ]
- ታሳፍራላችሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት?
- ለሥልጣን ብላችሁ አገር ትሸጣላችሁ?
- ማን ነው የሸጠው?
- እናንተው ናችኋ?
- አንተን መሰልንህ እንዴ?
- ማለት?
- አንተ እኮ ነህ ከጥቅምህ ውጪ ሌላ ነገር ማየት የማትችለው፡፡
- እ…
- አንተ አይደለህ እንዴ ያልሆነ ትርክት እየፈጠርክ ሕዝብ ከሕዝብ የምታባላው?
- ቢያንስ ከእናንተ እሻላለሁ፡፡
- በምን?
- እናንተ እኮ አገር እየሸጣችሁ ነው፡፡
- ከአንተ ብሶ እንዲህ ስታወራ አታፍርም?
- ምን ያሳፍረኛል?
- ለማንኛውም እናንተ መቃወም እንጂ መምራት የት ታውቁበታላችሁ?
- እልህ አያሲዙኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ማለት?
- እኔ የምሬን ከሠራሁ በዜሮ ነው የማስወጣችሁ፡፡
- ማን ከለከለህ?
- እናንተው ናችኋ፡፡
- ምን ብለን?
- አንተ መቃወም እንጂ መምራት አትችልም ብላችሁ ነዋ፡፡
- ታዲያ ዋሸን?
- እሱማ ትክክል ናችሁ፡፡
- ስለዚህ አርፈህ ተቃወም፡፡
- እኔ እኮ በመቃወም የሚገኘው ጥቅም በልጦብኝ እንጂ ጉድ ነበር የምሠራችሁ፡፡
- እ…
- ያው እናንተም ሥራ ስለምትሰጡኝ ብዬ እንጂ ድምጥማጣችሁን ነበር የማጠፋችሁ፡፡
- ከእኛ ጋር እንደምትሠራ ማውራት የለብህም ብዬሃለሁ፡፡
- እኔማ ለእርስዎ እንጂ ለሌላ ሰው አልናገርም፡፡
- ለማንኛውም አንተም አቅምህን ማወቅ አለብህ፡፡
- የምን አቅም?
- ከእኛ ጋር መወዳደር እንደማትችል ነዋ፡፡
- እሱን እንኳን ይተውት፡፡
- እንዴት?
- ምርጫውን ብወዳደር ድሮ እናንተ እንደምታሸንፉት ነበር የማሸንፈው፡፡
- በምንድነው የምታሸንፈው?
- በዝረራ!
[ለክቡር ሚኒስትሩ የቀድሞ ሚኒስትር ስልክ ደወሉላቸው]
- አላቆምም አላችሁ አይደል ክቡር ሚኒስትር?
- ምኑን?
- ብሽሽቁን ነዋ፡፡
- የምን ብሽሽቅ ነው?
- በየሄዳችሁበት ስለእኛ ብቻ ነው እንዴ የምታወሩት?
- ኧረ እኛ ብዙ ሥራ አለብን፣ ለወሬ ጊዜ የለንም፡፡
- የት እንደሚያደርሳችሁ ግን እናያለን፡፡
- መቼም አሁን የሚፈራችሁ እንደሌለ ታውቃለህ?
- እሱማ ጥርሳችን እንዳልተነቀለ ጠንቅቃችሁ ታውቃላችሁ፡፡
- ግን ያው ኬጅ ውስጥ ስላስቀመጥናችሁ ምንም አታመጡም፡፡
- ለማንኛውም እኛን ለማናደድ ብላችሁ የምታደርጉት ነገር መስመር እያለፈ ነው፡፡
- መስመር እያለፋችሁማ ያላችሁት እናንተ ናችሁ እኮ፡፡
- ምን አደረግን?
- የቱን ከየቱ ልዘርዝርልህ?
- እናንተስ ምን እያደረጋችሁ ነው?
- ምን አደረግን?
- ይኸው አርፈን እንዳንቀመጥ እያደረጋችሁን ነዋ፡፡
- እናንተ መቼ አርፋችሁ ተቀምጣችሁ ታውቃላችሁ?
- እ…
- እያንዳንዱን ሴራችሁን እናውቀዋለን፡፡
- ለማንኛውም ይኼ ብሽሽቅ እናንተን የትም አያደርሳችሁም፡፡
- እኛማ እናንተን እያበሸቅን አይደለም፡፡
- ታዲያ ምን እያደረጋችሁ ነው?
- እያወራረድን ነዋ፡፡
- ምን?
- ሒሳብ!