ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ትልቅ አበርክቶ ካላቸው ከተሞች ድሬዳዋ ትጠቀሳለች፡፡ ድሬዳዋ ካፈራቻቸው የቀድሞ ተጨዋቾች በቀድሞው መብራት ኃይል (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) ክለብ የሚታወቀው ስምዖን ዓባይ ከዓምና ጀምሮ ድሬዳዋ ከተማን በዋና አሠልጣኝነት ሲመራ ቆይቶ ከውጤት ጋር በተያያዘ ከኃላፊነቱ መነሳቱ ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13 ነጥብ ይዞ 14ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው የድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ክለብ፣ በፋይናንስ ዕጦት ቀውስ ውስጥ ከገቡ ክለቦች አንዱ መሆኑ ሲነገር ቆይቷል፡፡ ከፋይናንስ ቀውሱ በተጨማሪ በፕሪሚየር ሊጉ ቆይታውን አስጠብቆ በመቆየቱ ረገድም ፈተና ውስጥ ከገባ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡
የድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ክለብን ጨምሮ የክለቦች አመራሮች መገለጫ፣ ውጤት የመጨረሻ የመፍትሔ አማራጭ አድርገው የሚወስዱት አሠልጣኝ ማሰናበት እንጂ፣ ክለቦቻቸው ያሉባቸውን ክፍተቶች እንዲሁም ጠንካራና ደካማ ጎኖቻቸው ምን እንደሆነ ለማወቅ ጊዜውም ሆነ ዕውቀቱ እንደሌላቸው የሚናገሩ አሉ፡፡
የድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ክለብ ባለፈው ዓመት ስምዖን ዓባይን ዋና አሠልጣኝ አድርጎ ከመሾሙ በፊት በአሁኑ ወቅት የወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እግር ከስ ክለብ ዋና አሠልጣኝ ሆነው እየሠሩ የሚገኙት አሠልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ ይሁንና አሠልጣኙ ድሬዳዋን መልቀቃቸው የተሰማው የወራት ጊዜ እንኳ ሳይቆዩ ነው፡፡ የክለቡ አመራሮችም እስካሁን አሠልጣኙ የለቀቁበት ምክንያት ምን እንደሆነ ባያሳውቁም፣ በፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ጨዋታ ወደ ወላይታ ድቻ ያመራው ቡድናቸው በወላይታ ድቻ 2 ለ 0 መሸነፉ ሰበብ ሆኗል፡፡