በታላቅ የአገር ፍቅር ስሜት ተባብሮ መሥራት ከተቻለ ኢትዮጵያ ለመለወጥ፣ ለማደግና በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉ አገሮች ረድፍ ውስጥ ለመግባት የሚያቅታት አገር አይደለችም፡፡ ኢትዮጵያዊያን በሀቅ፣ በቅንነትና በጠንካራ የአንድነት መንፈስ ከተነሳሱ ምንም ነገር እንደማያቅታቸው ለማንም ግልጽ ነው፡፡ አገራቸውን ከወራሪዎች፣ ከተስፋፊዎችና ከቅኝ ገዥዎች የተከላከሉበት የጀግንነት ገድላቸው ብቻ ሳይሆን፣ አርቆ አሳቢነታቸውና አስተዋይነታቸውም ይመሰክራል፡፡ በጣም በርካታ ማንነቶች፣ ቋንቋዎች፣ ባህሎች፣ እምነቶችና የመሳሰሉት ልዩነቶች ሳይገድቧቸው ዘመናትን እየተሸጋገሩና በትውልዶች ቅብብሎሽ እዚህ መድረሳቸው፣ ዝንተ ዓለም የሚያስገርም የታሪካቸው አካል ነው፡፡ በተለያዩ ዘመናት በተነሱ ገዥዎች ጭቆናዎችና አፈናዎች ቢደርሱባቸውም እርስ በርስ እየተደጋገፉና እየተሳሰቡ፣ እንዲሁም በጋብቻ እየተዛመዱና እየተዋለዱ የጋራ መለያ የሆኑ አኩሪ እሴቶችን ገንብተዋል፡፡ ይህ አጭር ነገር ግን ማንም ሊክደው የማይችል የጥንታዊያን ኢትዮጵያዊያን መዘክር፣ በዚህ በሠለጠነ ዘመን ውስጥ በሚኖር ትውልድ የበለጠ ዳብሮና እመርታ አሳይቶ ኢትዮጵያን ታላቅ አገር የማድረግ ዓላማ ማስያዝ አለበት፡፡ ኢትዮጵያዊያን አንድ ላይ ሆነው በአገራቸው ጉዳዮች መምከር አለባቸው፡፡ ልዩነታቸውን ይዘው በአገራቸው ሁለንተናዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ ዓላማና ግብ እንዳላቸው ለዓለም ማሳየት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ልዩነትን ለውድድር ማቅረብ እንጂ የጠላትነት መሣሪያ ማድረግ የለባቸውም፡፡ ለፖለቲካ ሥልጣን የሚደረገው ፉክክር ማን የበለጠ ሠርቶ ኢትዮጵያን ያስከብራል እንጂ፣ አቅጣጫዋን አስቶ ገደል ውስጥ የሚከታት መሆን አይኖርበትም፡፡
ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ከ110 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ይኖርባታል ተብሎ ይገመታል፡፡ ይህንን ያህል የሕዝብ ቁጥር ያላት ትልቅ አገር በዕቅድ መመራት አለባት፡፡ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚና በማኅበራዊ መስኮች እጅግ በጣም አዋጭ የሆኑ የተመሰከረላቸው ፖሊሲዎች ተነድፈው፣ ለሥራ የደረሰው ሕዝቧ መሰማራት ይኖርበታል፡፡ ዕውቀት በመቅሰም ላይ ያሉ ወጣቶቿ ጥራት ያለው ትምህርት እንዲያገኙ፣ ከፍተኛ የሆነ ሁሉን አሳታፊ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት ማስፈን የግድ ይሆናል፡፡ ኢትዮጵያውያን በሠለጠነ መንገድ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸው መከበር አለባቸው፡፡ መብቶቻቸው የተከበሩላቸው ዜጎችም ኃላፊነት ተሰምቷቸው ግዴታቸውን መወጣት ይገባቸዋል፡፡ ሕግ አክባሪነትና አስከባሪነት የሁሉም ዜጎች ኃላፊነትና ግዴታ መሆን አለበት፡፡ በአገሪቱ የፖለቲካ ምኅዳር ውስጥ የሚሳተፉ ፖለቲከኞችም ሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ለሕጋዊና ለሰላማዊ የፖለቲካ ፉክክር ራሳቸውን ማስገዛት ይኖርባቸዋል፡፡ የሲቪክ ተቋማት፣ ቤተ እምነቶች፣ የትምህርት ተቋማት፣ የሙያና የጥቅም ማኅበራት፣ የዴሞክራቲክ ተቋማት፣ የተለያዩ ማኅበራትና የመሳሰሉት ኢትዮጵያ ውስጥ ሕግ እንዲከበርና ሕገወጥነት እንዲመክን ኃላፊነት እንዳለባቸው መገንዘብ አለባቸው፡፡ በተጨማሪም የፍትሕ አካላት፣ የፀጥታና የደኅንነት መዋቅሮች በሙሉ በተቻለ መጠን ገለልተኛ ሆነው ኃላፊነታቸውን የመወጣት ግዴታ እንዳለባቸው በፍፁም መዘንጋት የለባቸውም፡፡ ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት ይህ ዓይነቱ ጨዋነትና ክብር ነው፡፡ ሁሉም ነገር በሕግና በሥርዓት ሲከናወን ኢትዮጵያ ተስፋ ይኖራታል፡፡
በአሁኑ ጊዜ በጣም የተደበላለቁና ደስ የማይሉ ክስተቶች በብዛት ይስተዋላሉ፡፡ ብዙዎቹ ሆን ተብለው የሚፈጸሙ ድርጊቶች ሲሆኑ፣ በጣም ጥቂቱ ግን ባለማወቅ ወይም በቸልተኝነት የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያን የማደግ የተስፋ አቅጣጫ ከሚያስቱ ድርጊቶች መካከል አንዱ፣ ሐሰተኛ ወሬ በመንዛት መደናገር መፍጠር ነው፡፡ የሐሰተኛ ወሬዎች ዋና ዓላማ በኅብረተሰቡ ውስጥ ጥርጣሬና አለመተማመን በመፍጠር፣ የተለያዩ ፍላጎቶች ያሉዋቸውን ተፎካካሪዎች ወይም ተገዳዳሪዎች በማጣላት ደም ማቃባት ነው፡፡ በሰላማዊ መንገድ ለልዩነቶቻቸው ዕውቅና ተሰጣጥተው ለአገር ዕድገት አስተዋጽኦ ማበርከት የሚችሉ ኃይሎች ደም ሲቃቡ፣ አገር ሰላሟ እየተቃወሰና ዕድገቷ እያሽቆለቆለ ወደ ውድቀት ታመራለች፡፡ ይህ ዓይነቱ ክስተት ኢትዮጵያ ውስጥ ከመጠን በላይ ከመንሰራፋቱ የተነሳ፣ የሰዎች ባህሪ ከሰብዓዊነት ወደ አውሬነት እየተለወጠ ነው፡፡ ሰዎችን በድርጊታቸው ከመመዘን ይልቅ በብሔራቸው፣ በእምነታቸው፣ ወይም በተለያዩ ዝንባሌዎቻቸው ማጥቃት ወይም መወገን የተለመደ የክስረት መንገድ ሆኗል፡፡ ማንም ሰው የፈለገውን አቋም በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ ማራመድ መብቱ መሆኑ እየታወቀ፣ በጠላትነት መፈረጅና ከስም ማጥፋት እስከ አስከፊ ድርጊቶች መፈጸም የዘመናችን ነውር ተግባር ከሆነ ሰነባብቷል፡፡ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት የገነቡዋቸውን የተከበሩ የጋራ እሴቶች በመናድ፣ የገዛ ወንድምን በሚያራምደው አቋም ምክንያት እንደ አባትና እናት ገዳይ ማየት ደረጃ ላይ መደረሱ በጣም ያሳፍራል፡፡ እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ሠልጥኛለሁ ማለት ይቻላል? የገዛ ወገንን እንደ ቆሻሻ እየተፀየፉ አንድ ላይ መኖር ይታሰባል? በዚህ ሁኔታስ ኢትዮጵያ ወዴት እያዘገመች ነው? ይኼ በብርቱ ማነጋገር አለበት፡፡ ለኢትዮጵያ የማይጠቅማት ነውና፡፡
ኢትዮጵያዊያን ለአገር ደንታ በሌላቸውና ምናልባትም የታሪካዊ ጠላቶች ተላላኪ በሆኑ ኃይሎች የሚፈበረኩላቸውን አጀንዳዎች እስከ መቼ ሲያስተጋቡ ይኖራሉ? አገርን የምታህል የጋራ መኖሪያ ከዕለት ወደ ዕለት ሰላሟ እየተቃወሰና መላ ሕዝቧ እየተጨነቀ፣ የግለሰቦች ጉዳይ ከአገር በላይ ሆኖ በየቀኑ አጀንዳ የሚቀፈቀፈው ለምንድነው? ግለሰቦች ከሕግና ከአገር ህልውና በላይ ተደርገው የፖለቲካውን አየር ሲያጣብቡት ለምን አይባልም ወይ? ከ100 በላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሉባት በምትባል አገር ውስጥ የፖሊሲ አማራጮችን ከማዳመጥ ይልቅ፣ የግለሰቦች ውሎና አዳር ለምን ያስጨንቃል? አሉ ከሚባሉት ዩኒቨርሲቲዎች የተመረቁና የሚያስተምሩ ልሂቃን ጭምር ስለፖሊሲ አማራጮች መቅረብ መሞገት ሲገባቸው፣ የአንድ ግለሰብ ዜግነት ማግኘትና አለማግኘት ለምን ይሆን እንቅልፍ የሚነሳቸው? የዜግነት ጉዳይ በሕግ ተደንግጎና የአፈጻጸም ሥርዓቱ በግልጽ እየታወቀ፣ ልክ እንደ አላዋቂ በፋይዳ ቢስ ጉዳይ ላይ የራስንም ሆነ የሌሎችን ጊዜ ማባከን ምን የሚሉት ዕውቀት ይሆን? ኢትዮጵያ ከፊቷ በርካታ መፍትሔ የሚፈልጉ አንገብጋቢ ጉዳዮች ተደቅነውባት፣ አቅጣጫ የሚያስቱ ትርኪምርኪ ነገሮች ውስጥ ተዘፍዝፎ ውሎ ማደር ምን የሚሉት በሽታ ነው? በጣም የሚያሳዝነው ደግሞ እናውቃለን፣ ተምረናል፣ በቅተናል፣ ካለኛ ማን አለ፣ ወዘተ የሚሉ የዚህ ውጥንቅጥ ሰለባ መሆናቸው ነው፡፡ ይህ ፈጽሞ ኢትዮጵያንም ሕዝቧንም አይጠቅምም፡፡ ለዚህ የሠለጠነ ዘመን የማይመጥን ኋላቀርነት ነው፡፡
ዘወትር እንደምንለው ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ ያላት አገር ናት፡፡ ይህን ተስፋ የማለምለምና ወደ ውጤት የመቀየር ኃላፊነት የኢትዮጵያዊያን ብቻ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን አንድ ላይ ለአንድ የጋራ ብሔራዊ ዓላማ መቆም ሲችሉ፣ ተዓምር መሥራት እንደማያቅታቸው የዓለም ጥቁር ሕዝቦች መኩሪያ የሆነው ታላቁ ፀረ ኮሎኒያሊስት የዓድዋ ጦርነት ድል ምስክር ነው፡፡ ይህ በዘመኑም ሆነ ከዚያ በኋላ ባሉ ዓመታት ዓለም በታላቅ አክብሮት የሚዘክረው ድል፣ ኢትዮጵያዊያን መተባበር ከቻሉ ምንም እንደማያቅታቸው ህያው ምስክር ነው፡፡ ማንም ሊያስተባብለው የማይቃጣው ሀቅ ነው፡፡ በአሁኑ ዘመን የተኳረፉትን የማቀራረብ፣ የማይነጋገሩትን በግንባር በማገናኘት የማወያየት፣ ዓይንህ ለአፈር የተባሉትን ዓይን ለዓይን የማገጣጠም፣ በአጠቃላይ በአንድ ጣራ ሥር መገናኘት የማይፈልጉትን በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ የማገናኘት፣ ወዘተ በጎ ጅምሮች ለአገር በሚያስቡ የተለያዩ አካላት እየታዩ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን ለጊዜው እንጂ መገናኘትና መነጋገር ሲጀምሩ ለያዥ ለገናዥ እንደማያስቸግሩም ምልክቶችን ማየት ተችሏል፡፡ ጊዜያዊ እልህ፣ ንዴት፣ ቁጣና ቂምን ወደ ጎን ብሎ ወንድም ከወንድሙ፣ እህት ከእህቷ ተገናኝተው የመነጋገራቸው ጅምር ይበል መባል ይገባዋል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች የተሰማሩ ወገኖችም ከሐሰተኛ ወሬዎች ቢታቀቡና ገንቢ ተግባራት ላይ ቢያተኩሩ፣ እየተገኘ ያለው ተስፋ ወደር ወደሌለው ውጤት መሸጋገሩ አይቀርም፡፡ ኢትዮጵያዊያንም የሚያምርባቸው ይህ ዓይነቱ ሥልጡን መንገድ ስለሆነ፣ ቅንነት በተሞላበት መንፈስ መቀራረቡን ይልመዱ፡፡ ያኔ ኢትዮጵያ ወደ ዕድገት የምታደርገው ጉዞ በልጆቿ ትብብር ቀና ይሆናል፡፡ ለዚህ ሲባል ነው ኢትዮጵያን አቅጣጫዋን ከሚያስቱ አደገኛ ድርጊቶች መታደግ ያለብን!