በጌታቸው ይልማ (ኢንጂነር)
በእስራኤልና በግብፅ መካከል እ.ኤ.አ. በ1973 የተከሰተውን የዮም ኪፑር ጦርነትን አሜሪካና የምዕራቡ ዓለም አገሮች ለእስራኤል ወግነዋል በሚል መነሻነት፣ ነዳጅ አምራች የሆኑ የዓረብ አገሮች በአሜሪካና በምዕራቡ አገሮች ላይ በጣሉት ነዳጅን ያለመሸጥ ማዕቀብ ምክንያት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በአራት እጥፍ በማደጉ የኢኮኖሚ ቀውስ ተከስቶ ነበር፡፡ ከነዳጅ ውጭ ያሉ ሁሉንም የኃይል አማራጭ ምንጮችን ማበልፀግና መጠቀም አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን የአገሮች የደኅንነት ጉዳይ መሆኑን ምዕራባውያን ተገንዝበው ትልቅ ትኩረት በመስጠት ሠርተዋል፣ አሁንም በመሥራት ላይ ይገኛሉ፡፡
ከእነዚህ አማራጭ የኃይል ምንጮች መካከል የኑክሌር ኤሌክትሪክ ኃይል ዩራኒየም የተሰኘውን ቁስ አተም፣ በማብላያ ውስጥ ወደ ትናንሽ ቅንጣቶች እንዲከፋፈል በማድረግ የሚገኘው ከፍተኛ ሙቀት ውኃን እንዲያፈላ በማድረግ፣ ተርባይኖችን ሲያሽከረክር የሚገኝ የኤሌክትሪክ ኃይል አንዱና አስተማማኙ ነው። ከኤሌክትሪክ ማመንጫነት ባለፈ የኑክሌር ኃይል ለኢንዱስትሪ አገልግሎት፣ ለግብርና ምርት ማሳደጊያነት፣ ለሕክምና አገልግሎትና ለጥናትና ምርምር ሥራዎች በዋነኛነት ጥቅም ላይ ውሏል። የኑክሌር ኤሌክትሪክ ኃይል ከፍተኛ ኃይል የማመንጨት አቅም ያለው ሲሆን በአሜሪካ በተደረገ ጥናት በአማካይ 92.3 በመቶ በዓመት ውስጥ ሳይቆራረጥ የማመንጨት አቅም (capacity factor) እንዳለው ተረጋገግጧል፡፡ ይህም ማለት በዓመት ውስጥ ካሉት 365 ቀናት ውስጥ ያለምንም መቆራረጥ ለ336 ቀናት ኃይል አመንጭቷል ማለት ሲሆን 29 ቀናቱም ለጥገና የተወሰደ ጊዜ ነው፡፡ በሌላ በኩል አገራችን በስፋት የምትጠቀምበትን የውኃ ኃይል ማመንጫን ብንመለከት ያለማቋረጥ የማመንጨት አቅሙ 38.2 በመቶ ብቻ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በዚህ ሥሌት መሠረት ካሉት 365 ቀናት ውስጥ 138 ቀናት ብቻ ኃይል መስጠት እንደሚችል በግልጽ አሳይቷል፡፡
ይሁንና ኑክሌርን እጅግ የሚፈራና ጥብቅ ቁጥጥር እንዲደረግበት ያስገደደው ለመጀመሪያም ለመጨረሻም ጊዜ እ.ኤ.አ. በ1945 በሁለቱ የጃፓን ከተሞች በጦር መሣሪያነት ውሎ 80,000 በሂሮሺማ 70,000 ደግሞ በናጋሳኪ የሰዎችን ሕይወት ከቀጠፈ በኋላ ነው። ሌላው አሉታዊ ገጽታ እንዲኖረው ያደረገው እ.ኤ.አ በ1986 ከጥንቃቄ ጉድለት የተነሳ ከሩሲያው የቼርኖቤል የኑክሌር ጣቢያና እ.ኤ.አ በ2011 ከጃፓኑ የፋኩሺማ የኑክሌር ኃይል ጣቢያ ሱናሜን ተከትሎ በተፈጠረ የጨረር ማፈትለክ ምክንያት በሰውና በንብረት ላይ ያደረሱት አደጋዎች በኑክሌር ኃይል አጠቃቀም ላይ በዋነኛነት ጠባሳ ጥለው አልፈዋል።
እነዚህ ተግዳሮቶች ቢኖሩም የኑክሌር ኃይልን ለኤሌክትሪክ ማመንጫነት መጠቀም ባደጉትም ሆነ በማደግ ላይ ባሉት አገሮች ተጠናክሮ ቀጥሎ ወደ አሥር በመቶ የሚጠጋውን የዓለም ኤሌክትሪክ ፍላጎትን ያሟላል። በዓለም ላይ በአሁኑ ጊዜ በ31 አገሮች 417 የኑክሌር ማብላያዎች ያሉ ሲሆን፣ ከእነዚህም እ.ኤ.አ በ2018 ብቻ 2,563 ቴራ ዋት አወር የኤሌክትሪክ ኃይል መንጭቷል። አሜሪካ ከፍተኛ የኑክሌር ኃይል በስፋት የምትጠቀም ሲሆን ቻይና በበኩሏ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ያለ የኑክሌር ኃይል ልማት ፕሮግራም ያላት አገር ናት። የዓለም አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ እንዳሳወቀው በአሁኑ ወቅት የኑክሌር ኃይልን ለማልማት ከሚፈልጉ የዓለም አገሮች አንድ ሦስተኞቹ የአፍሪካ አገሮች ናቸው። ከነዚህም አገሮች መካከል አልጄሪያ፣ ሞሮኮ፣ ቱኒዚያ፣ ግብፅ፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ዑጋንዳ፣ ዛምቢያ፣ ኒጀር፣ ናይጄሪያና ሱዳን በዋናነት ይጠቀሳሉ። የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚያሳስቡት አፍሪካ በማደግ ላይ ላለው ኢኮኖሚዋና የሕዝብ ቁጥሯ ይህንን የኃይል አማራጭ መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ያስገነዝባሉ። ሌላው ለአፍሪካ መልካም አጋጣሚ የሆነው 20 በመቶ የዓለማችን የዩራኒየም ክምችት በአኅጉሪቱ መገኘቱ ነው። 34 የአፍሪካ አገሮች መጠኑ ይለያይ እንጂ የዩራኒየም ማዕድን ክምችት ያላቸው መሆኑ ለኑክሌር ኃይል ልማት አንዱ ምቹ መደላድል ሊሆን ይችላል። የኑክሌር ኃይል ባለቤት መሆን የአንድን አገር ዘመናዊነትን በማጉላት ተቀባይነትን ከሚጨምሩ ጉዳዮች አንዱ ሲሆን የአገሪቱን የኢኮኖሚ ሁኔታ፣ መረጋጋትንና የዕድገት ደረጃ አመልካች ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል።
ኢትዮጵያን በተመለከተ እ.ኤ.አ. 2014 ዓ.ም. በወጣ ረቂቅ የኢነርጂ ፖሊሲ ላይ ኑክሌርን እንደ አንድ የኃይል ምንጭነት ለመጠቀም ታቅዶ ነበር። ከሦስት ዓመታት ቆይታ በኋላ ኑክሌር ለማልማት ኢትዮጵያ ከሩሲያ ጋር የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረመች ቢሆንም በዘርፉ የታየ እመርታ አልነበረም። በድጋሚ እ.ኤ.አ. 2019 ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ በሶቺ በነበረው የሩሲያና የአፍሪካ የኢኮኖሚ ፎረም ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት ኢትዮጵያ ለምታደርገው የኑክሌር ኃይል ልማት ሩሲያ የቴክኖሎጂና የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ለማገዝ በአሥር ዓመታት ውስጥ ዕውን እንዲሆን የሚያስችል የስምምነት ማዕቀፍ የተፈራረሙ ቢሆንም እስካሁን የታየ ተጨባጭ ነገር ያለመኖሩ ለጉዳዩ ትኩረት እንዳልተሰጠው ያመለክታል።
እንዲህ ያሉ ከሥልጣኔና ቴክኖሎጂ ጋር የተያያዙ መዘግየቶች ቸል ከተባሉ አገሪቱን ወደ ኋላ የሚጎትት ብቻ ሳይሆን አሁን ባለው የዓለም የቴክኖሎጂ ውድድርና ዕድገት ዋጋ የሚያስከፍል እንዳይሆን መጠንቀቅ ይገባል። ለዚህ እንደ አንድ ማሳያ ለመጥቀስ ኢትዮጵያ በቅርቡ ወደ ህዋ ያመጠቀችው የመጀመሪያው ሳተላይት አገሪቱ ከሚያስፈልጋት የዕድገት ግስጋሴ አንጻር በጊዜ እጅግ የዘገየ ከቁጥር አንጻር በርካታ ሳተላይቶች ያስፈልጓት እንደነበር ስንገነዘብ ፈጥነን መራመድ ካልቻልን ሁሌም ተማሪዎች እንደሆንን እንቀጥላለን። መልካሙ አጋጣሚ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ለቴክኖሎጂና ሥልጣኔ ያላቸው ብርቱ ፍላጎት የኑክሌርንም ኃይል ለማበልፀግ የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ቢያግዟቸው አመቺ ሁኔታዎችን ይፈጥራል የሚል ግምት አለኝ። ከሩሲያ ጋር የተደረገውን ስምምነት ተግባራዊ ለማድረግ ጠንካራ ክትትል በመንግሥት ደረጃ ማድረግ አስፈላጊ ሲሆን ሌሎች በዘርፉ ልምድ ያላቸውን አገሮች እንደ ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ እንግሊዝ ከተቻለም አሜሪካን ጨምሮ ድጋፎችን የማሰባሰብ ጉዳዮችን በመንግሥት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሠራት ይኖርበታል።
በመሆኑም የኑክሌር ልማቱን በኢትዮጵያ ዕውን ለማድረግ በቀጣይ የኑክሌር ልማት ፖሊሲና የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት፣ የዩራኒየም ማዕድን ክምችት በአገሪቱ መኖር አለመኖሩን ማረጋገጥ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በሚገኘው የፊዚክስ ትምህርት ክፍል በሁለተኛና በሦስተኛ ዲግሪ ደረጃ ለማሠልጠን የሚያስችል የትምህርት ካሪኩለም መቅረፅ፣ እንደዚሁም በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሥር ለኑክሌር ልማት ብቻ የተለየ ጠንካራ ክፍል በማደራጀት ክትትልና ድጋፍ ማድረግ ወሳኝ ተግባራት ሊሆኑ ይገባል።
የኑክሌር ኃይል ልማት ቀድሞ ከነበረበት የዕድገት ደረጃ ከፍተኛ መሻሻል የታየበት የሳይንስ ዘርፍ በመሆኑ፣ አገራችን ይህንን የለማ የቴክኖሎጂ ደረጃ ከኋላ ተነስቶ የመጠቀምና የማላመድ መልካም አጋጣሚ ከተጠቀሱት አገሮች ጋር ባለን የመንግሥት ለመንግሥት ግንኙነቶች፣ እንደ አንድ ዋነኛ አጀንዳ በመያዝ ድጋፎችን አጠናከሮ የማፈላለግ ሥራ ሊተኮርበት ይገባል። በዘርፉ የሰው ኃይል ልማትን ዕውን ለማድረግ በፊዚክስ ልዩ ችሎታ ያላቸውን ተመራማሪዎችን በማሰባሰበ በአገር ውስጥና በውጭ አገሮች ለማሠልጠን ርብርብ ማድረግ ያስፈልጋል። በመሆኑም አገሪቱ ያላትን አረንጓዴ መር የኢኮኖሚ ፖሊሲና ዓለም አቀፍ የኑክሌር ኃይል አጠቃቀም ሕግጋትን ከግንዛቤ ያስገባ የኑክሌር ኃይል ልማት ፕሮግራም ቀርፆ መንቀሳቀስ ለነገ የሚባል ሥራ ያለመሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል።
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected]. ማግኘት ይቻላል፡፡