ለካሜሮኑ የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያውን እያከናወነ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) በመጋቢት ሁለተኛ ሳምንት መደበኛ ልምምድ እንደሚጀምር የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል፡፡ ቡድኑ አይቮሪኮስት፣ ማዳጋስካርና ኒጀር ከሚገኙበት ምድብ ሦስት ነጥብ ይዞ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ፣ ማዳጋስካር በስድስት ነጥብ ምድቡን ትመራለች፡፡
ኢትዮጵያ በምድብ ማጣሪያው የመጀመርያ ጨዋታ ከሜዳዋ ውጪ በማዳጋስካር አንድ ለዜሮ ከተሸነፈች በኋላ በሁለተኛው ማጣሪያ በአፍሪካ እግር ኳስ ደረጃዋ በትልቁ ከምትጠቀሰው አይቮሪኮስት ጋር በባህር ዳር ስታዲየም ተጫውታ ሁለት ለአንድ በሆነ ውጤት ማሸነፍ መቻሏ ለ2021 የካሜሮን የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ መነሳሳት ፈጥሮላታል፡፡
የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የማጣሪያ ጨዋታ መርሐ ግብር እንደሚያስረዳው ከሆነ፣ ሦስተኛውን የምድብ ጨዋታ በመጋቢት ወር መጨረሻ ይደረጋል፡፡ በዚሁ መሠረት ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፉና ለአኅጉራዊ ውድድሮች በተፈቀደላት ብቸኛው የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ከምድቡ ሁለት ጨዋታዎችን ከተሸነፈችው ኒጀር ጋር ትጫወታለች፡፡
ለዚህም ሲባል በዚህ ሳምንት የተጀመረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ዙር የጨዋታ መርሐ ግብር የሚቋረጥ መሆኑን ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡ በሌላ በኩል በትውልድ ኢትዮጵያዊ የሆኑና በተለያዩ የአውሮፓና ሌሎች አገሮች የሚጫወቱ ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለመጫወት ፍላጎት ቢኖራቸውም፣ ዜግነትን የሚመለከተው የአገሪቱ ሕግ አስቸጋሪ እንደሆነባቸው እየተነገረ ይገኛል፡፡