አቶ ጋሻው የትዋለ ከአስመራ ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ሲያገኙ፣ ኔዘርላንድስ ከሚገኘው ማስትሪች ስኩል ኦፍ ማኔጅመንት በፕሮጀክት አፕሬዛል፣ እንዲሁም ማኔጅመንት ዲፕሎማ፣ አውስትራሊያ ከሚገኘው የካንቤራ ዩኒቨርሲቲ በዓለም አቀፍ የታክስ አስተዳደር የማስተርስ ዲግሪ አግኝተዋል፡፡ በማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲዎች፣ በኮርፖሬት ቢዝነስ ስትራቴጂ፣ በፕሮጀክት ፕላኒንግና ማኔጅመንት በርካታ ሥልጠናዎች ተከታትለዋል፡፡ በኢንግሊዝ፣ በኔዘርላንድስና በቤልጂየም፣ እንዲሁም በአፍሪካ በኡጋንዳ፣ በደቡብ አፍሪካ፣ በኬንያና በታንዛኒያ የተከታተሏቸው የአጭርና የመካከለኛ ጊዜ የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን መውሰዳቸውን ይናገራሉ፡፡ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲዎችንና የኮርፖሬት ቢዝነስ ስትራቴጂዎችን በዋናነት የንግድ፣ የታክስ፣ የፋይናንስ፣ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ጉዳዮች ላይ የዳበረ ልምድ አላቸው፡፡ በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ክልሎችን በመወከል፣ ከዓለም ባንክና ከዓለም የገንዘብ ድርጅት የጥናትና የባለሙያዎች ቡድን ጋር በቅርበት በመሥራት፣ የአገሪቱን የታክስና የፋይናንስ ጉዳዮች ከአገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገትና ልማት አንፃር በማጥናትና በመገምገም የፖሊሲ ሐሳቦችንና ስትራቴጂዎች ላይ የዳበረ ልምድ አላቸው፡፡ የኢትዮጵያን የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ፕሮጀክት በማዘጋጀትና ፕሮግራሙን በመምራት፣ እንዲሁም እንዲተገበር በማስተባበር ተሳትፈዋል፡፡ በአጠቃላይ ከ27 ዓመታት በላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲዎችንና የኮርፖሬት ስትራቴጂዎችን ከማመንጨት ልምዳቸው በመነሳት፣ የኢትዮጵያ የዳያስፖራ ባንክ አክሲዮን ማኅበርን ከሐሳብ ጀምሮ አሁን እስከሚገኝበት ደረጃ ድረስ በአደራጅነትና በመሥራችነት የሚሳተፉት አቶ ጋሻው፣ የሚመሠረተው የዳያስፖራ ባንክ ዓላማዎቹንና የወደፊት እንቅስቃሴዎቹን በተመለከተ ብርሃኑ ፈቃደ አነጋግሯቸው የሚከተለውን አጠናቅሯል፡፡
ሪፖርተር፡– የኢትዮጵያ የዳያስፖራ ባንክ ማቋቋም ለምን አስፈለገ?
አቶ ጋሻው፡– ከማክሮ ኢኮኖሚ የዕድገትና ልማት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች አንፃር ፈጣን፣ ዘላቂነትና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገትና ልማት በማምጣት የአገሪቱን የመካከለኛ ገቢ ራዕይ እ.ኤ.አ. በ2025 ዕውን ለማድረግ ሲታሰብ፣ በአንድ በኩል የአገሪቱ ማክሮ ኢኮኖሚ እየጨመረ መምጣቱ በሌላ በኩል ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት መኖሩ፣ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክን ለማቋቋም እንደ ዋና ገፊ ምክንያት ተደርጎ ተወስዷል፡፡ በመንግሥት አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም የማክሮ ኢኮኖሚው ቁልፍ ችግር የውጭ ምንዛሪ እጥረት መሆኑ በጥናት ተረጋግጧል፡፡ የማክሮ ኢኮኖሚ አመልካቾችን በተመለከተ የፊስካል ፖሊሲውና የሞኒተሪ ፖሊሲው መስተጋብር የተጣጣመ አለመሆን ዋናው ቁልፍ ችግር ሲሆን፣ በዚህ ረገድ በተለይ የወለድ ምጣኔ፣ የዋጋ ግሽበት ምጣኔ፣ የቁጠባ ምጣኔ፣ የታክስ ምጣኔ፣ የኢንቨስትመንት ምጣኔ፣ የጉልበትና የገበያ ዋጋ ምጣኔና የጥቁር ገበያ ምጣኔ፣ የተጣጣመና የተመጣጣነ አለመሆን ነው፡፡ በአጠቃላይ የምርት ፍላጎትና አቅርቦት፣ የገንዘብ አቅርቦትና ፍላጎት፣ የውጭ ምንዛሪ አቅርቦትና ፍላጎት የተጣጣመና የተመጣጣነ አለመሆን የማክሮ ኢኮኖሚው ቁልፍ ችግር ነው፡፡ በመሆኑም የአገሪቱን የኢኮኖሚ ምኅዳርና የውጭ ምንዛሪ ቋት ለማስፋት የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ አክሲዮን ማኅበርን ማቋቋም አስፈልጓል፡፡
በሌላ በኩል አንዱ ቁልፍ ችግር የድህነት ጉዳይ ሲሆን፣ በዚህ ረገድ ዝቅተኛ ገቢ ዝቅተኛ ቁጠባ፣ ዝቅተኛ ቁጠባ ዝቅተኛ ኢንቨስትመንት፣ ዝቅተኛ ኢንቨስትመንት ዝቅተኛ ገቢ የሆነውን የድህነት አዙሪት አከርካሪውን ለመስበር መሠረተ ሰፊ የሆኑ አዋጭ የኢኮኖሚ ዘርፎችን ፋይናንስ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ክምችትን ለመጨመር፣ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ አክሲዮን ማኅበርን ለማቋቋም አስፈልጓል፡፡ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት የዓለም ኢኮኖሚ ከግብርና መር ወደ ኢንዱስትሪ መር፣ ከኢንዱስትሪ መር ወደ አገልግሎት ዘርፍ መር፣ አገልግሎት ዘርፍ መር ወደ ቴክኖሎጂ ዘርፍ መር፣ ከቴክኖሎጂ ዘርፍ መር ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ መር በፍጥነት በመሸጋገር ሒደት ላይ ይገኛል፡፡ በመሆኑም በአሁኑ ወቅት አገሪቱ የጀመረችውን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ የለውጥ ጉዞ ወደፊት ማራመድ ያስፈልጋል፡፡ በተለይ የብልፅግና ጉዞን ወደፊት ለማራምድና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ አብዮት በማቀጣጠል ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ሽግግር በፍጥነት ለማምጣት የትውልደ ኢትዮጵያውያውን ዳያስፖራዎች የልማት ተሳትፎ በባንኩ ምሥረታ ጉልህ ሚና የሚጫወት መሆኑ ከዓለም አቀፍና አኅጉር አቀፍ ተለዋዋጭ የኢኮኖሚ ሁኔታ አንፃር፣ በተለይም ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን በሒደት ላይ የምትገኝ ስለሆነ ሰጥቶ በመቀበል መርህ የማክሮ ኢኮኖሚ የፋይናንስ ዘርፉን ደረጃ በደረጃ ለነፃ ገበያው በሯን ክፍት በማድረግ፣ ተጠቃሚነቷን ሙሉ በሙሉ ለማረጋገጥ ባንኩን ማቋቋም አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡
ለባንክ ኢንዱስትሪያችን የቴክኖሎጂ ፍላጎት በ21ኛው ክፍለ ዘመን ዓለም የደረሰችበትን ከፍተኛ የባንክ ኢንዱስትሪ የቴክኖሎጂ ደረጃ በመተግበር የደንበኞችን እርካታ ማሳደግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ የባንክ ኢንዱስትሪውን የፈጠራና የሙያ ብቃት ጥራት ፍላጎት፣ የባንክ ኢንዱስትሪው ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የሙያ ብቃትና ጥራት የሚፈልግ ከመሆኑ አንፃር ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን በጠበቁ ቅን ታማኝና ተጠያቂ አመራሮችና ባለሙያዎች በማደራጀትና በማሰማራት፣ አዲስ ባንክ ማቋቋም አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡ ስፔሻላይዜሽንና ዳይቨርሲፊኬሽን (ብዝኃነት) በማስፈለጉ ከከፍተኛና መሠረተ ሰፊ በሆኑ ውስን የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ የተመሠረተ ሁሉን አቀፍ ባንክ ማቋቋም በማስፈለጉ ነው፡፡ ከፍተኛ የውጭ ምንዘሪ ፍላጎት ያላቸውን ግዙፍ የኢኮኖሚ ዘርፎች ፋይናንስ ማድረግ በማስፈለጉ፣ በዚህ ረገድ ግዙፍና መሠረተ ሰፊ የሆኑ ኢንዱስትሪዎችን ማለትም የህዋ ሳይንስ ቴክኖሎጂ፣ የሳይበር ቴክኖሎጂ፣ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ፣ የሕክምና ኢንዱስትሪ፣ የኃይል ኢንዱስትሪ፣ የፊልም ኢንዱስትሪ፣ የግብርና ኢንዱስትሪና የምሥራቅ አፍሪካ የመሠረተ ልማትን ፋይናንስ ለማድረግ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ ከሌላው መደበኛ ባንክ በምን ይለያል?
አቶ ጋሻው፡– የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ ከስያሜው ጀምሮ ዳያስፖራውን የሚመለከት ሲሆን፣ ከ70 በመቶ በላይ ዳያስፖራው ላይ አተኩሮ የሚሠራ ይሆናል፡፡ ባንኩ ለዳያስፖራው የአገሩ የኢኮኖሚ ልማት ዓርማ ወይም ምልክት በመሆን፣ ዳያስፖራው በአገሩ ዕድገትና ልማት ከፍተኛ ተሳትፎ በማድረግ አገሪቱ ከድህነት ቀለበት ለመውጣት የምታደረገውን እልህ አስጨራሽ መራራ ትግል አከርካሪውን ለመስበር በሚደረገው ጉዞ ዘመን ተሸጋሪ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ ጥናቶች ኢንደሚያመለክቱት አገሮች እንደ ራሳቸው የመንግሥት አወቃቀርና የኢኮኖሚ ፖሊሲ ኢኮኖሚያቸውን ጥቃቅን፣ አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ በማለት ይከፋፍላሉ፡፡ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክን ለመመሥረት አራት አማራጮች ቀርበዋል፡፡ የመጀመሪያው አማራጭ ከጥቃቅን ጀምሮ ሁሉንም የኢኮኖሚ ዘርፎች ማካተት፣ ሁለተኛው አማራጭ መካከለኛውን የኢኮኖሚ ዘርፍ ማካትት፣ ሦስተኛው አማራጭ ከፍተኛውን የኢኮኖሚ ዘርፍ መሠረት ማድረግና አራተኛው አማራጭ የመካከለኛውንና የከፍተኛውን የኢኮኖሚ ዘርፍ ውህድ በመውሰድ ማደራጀት የሚል ነው፡፡
በዚህ ረገድ በተካሄደው ጠቋሚ ጥናት መሠረት የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ መካከለኛውንና ከፍተኛውን አወቃቀር የሚመለከት ይሆናል፡፡ በኢኮኖሚው ዑደት ውስጥም መካከለኛና ከፍተኛ ገቢ ያላቸውን የኢኮኖሚ ተዋንያን የሚመለከት ይሆናል፡፡ ባንኩን ትርፋማ የሚያደርጉና አዋጭ ሜጋ መሠረተ ሰፊ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ አተኩሮ የሚሠራ በመሆኑ፣ በኢኮኖሚ ትስስር ሒደት ዝቅተኛውን የኅብረተሰብ ክፍልን ጨምሮ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ የሚያደርግ ይሆናል፡፡ የተፈቀደ ካፒታል ስድስት ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ የተመዘገበ ካፒታል አራት ቢሊዮን ብር ይሆናል፡፡ ዝቅተኛው የአክሲዮን ሽያጭ መጠን ብር 200 ሺሕ ብር መሆኑ፣ ከአሁን በፊት አክሲዮን ይሸጡ ከነበሩት ባንኮች ሁሉ የተለየ ያደርገዋል፡፡ ‹ከስፔሻላይዜሽን፣ ከዳይቨርስፊኬሽን፣ ከሴግመንቴሽን፣ ከምርምር፣ ከቴክኖሎጂና ከሙያ ብቃት› አንፃር ባንኩ የተለያዩ አሠራሮችን ይዞ ይቀርባል፡፡ ከዚህ አኳያ ከሕግ ማዕቀፍ አንፃርም የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ በአዋጅ ቁጥር 1159/2011 እና አፈጻጸም መመርያ ቁጥር ssb /73/2020 የውጭ ዜግነት ባላቸው ትውልደ ኢትዮጵያውያንና ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያውያን በሆኑ ባለሀብቶች፣ የውጭ ዜግነት ባላቸው ትውልደ ኢትዮጵውያንና ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች የተያዙ የሕግ ሰውነት ባላቸው ኩባንያዎች ይመሠረታል፡፡
ሪፖርተር፡– ከዳያስፖራው ሊሰበሰብ ከታሰበው ካፒታል በተጨማሪ ዳያስፖራው በምን መንገድ ሊሳተፍ ይችላል?
አቶ ጋሻው፡– ባንኩ ዓለም የደረሰችበትን ከፍተኛ የባንክ ኢንዱስትሪ ቴክኖሎጂ የሚተገብር ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ዳያስፖራው የባንክ ቴክኖሎጂ የልቀት ማዕከል እንዲሆን ቅድሚያ ዕድሉ ይሰጠዋል፡፡ እንደሚታወቀው አብዛኞቹ በሥራ ላይ ያሉ ባንኮች ቴክኖሎጂ የሚገዙት ከህንድና ከቻይና ከመሳሰሉት አገሮች በመሆኑ፣ ወደፊት በምሥረታ ሒደት ላይ ላሉ ባንኮችም ጭምር የቴክኖሎጂ ምንጭ በመሆን የውጭ ምንዛሪ ከማስቀረቱም በላይ፣ ኩባንያ በመፍጠር ሰፊ ተሳትፎ እንዲኖረው ይበረታታል፡፡ በሌላ በኩል የባንክ ኢንዱስትሪው ዘርፍ ደረጃውን የጠበቀ የሙያ ጥራትና ብቃት የሚያስፈልገው በመሆኑ፣ ዳያስፖራው ባንኩን በማማከር እንዳስፈላጊነቱ የአገሪቱ ሕግ በሚፈቅደው መሠረት ተቀጣሪ በመሆንና ኩባንያ በመፍጠር የአጭር፣ የመካከለኛና የረዥም ጊዜ ሥልጠና በመስጠት የዘርፉ የልዕቀት ማዕከል እንዲሆን ይበረታታል፡፡
ሪፖርተር፡– ሊመሠረት የታሰበው ባንክ የተፈቀደ ወይም የታቀደ ካፒታል ስድስት ቢሊዮን ብር ነው፡፡ ዳያስፖራው ይህን ያህል ገንዘብ ሊያዋጣ እንደሚችል ምን መተማመኛ አለ?
አቶ ጋሻው፡– ባካሄድነው ጠቋሚ ጥናት ከሦስት ሚሊዮን በላይ ዳያስፖራዎች በውጭ እንደሚኖሩ ሲታሰብ፣ ከስድስት ቢሊዮን ዶላር በላይ ወደ አገራቸው በዓመት እየላኩ በመሆናቸው፣ ይህ አቅም ባንኩን ለማቋቋም ታሳቢ ተደርጓል፡፡ በዚህ ረገድ በተለይ ባንኩ ቁጥራቸው ከአንድ በመቶ በታች በሆኑ መካከለኛና ከፍተኛ ገቢ ባላቸው ባለሀብቶች ላይ አተኩሮ ይሠራል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት በዓለም ባንክና በዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ትንበያ መሠረት፣ እ.ኤ.አ. በ2020 ከስድስት በመቶ በላይ እንደሚሆን ስለተነበየና በምሥራቅና በመካለኛው አፍሪካ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ግዙፍ እንደሆነ በመረጋገጡ፣ የአገር ውስጥ መካከለኛና ከፍተኛ ገቢ ያላቸው ባለሀብቶች ሰፊ ተሳትፎ እንደሚኖራቸው ባደረግነው ቅድመ ጥናት በመረጋገጡ፣ ከአክሲዮን ሽያጭ አንፃር የተጠቀሰውን ካፒታል ለማሳካት ዝቅተኛ የአክሲዮን ብዛት አሥር ወይም 200 ሺሕ ብር ሲሆን፣ 60 በመቶ በቅድሚያ የሚከፈልና ቀሪው በሁለት ጊዜ ክፍያ የሚፈጸም በመሆኑ፣ በውጭ ምንዛሪም ክፍያው አዋጭ መሆኑ የጥናት ታሳቢዎች ያመለክታሉ፡፡
ሪፖርተር፡– ከዚህ ቀደም መንግሥት ባሻው ጊዜ ሕግ ሲያወጣና ሲቀይር በዳያስፖራው ላይ በርካታ ችግሮች ተፈጥረዋል፡፡ ወደፊትስ እንዲህ ያለው ነገር ላለመምጣቱ ምን ዓይነት ዋስትና ይኖራል?
አቶ ጋሻው፡– ከለውጡ ቀደም ብሎ በነበረው ሥርዓት ዳያስፖራው አክሲዮን እንዳይገዛ መደረጉ፣ የገዛውንም እንዲሸጥ መገደዱ ምንም ዓይነት የኢኮኖሚ ገፊ ምክንያት የለም፡፡ የዓለም ተሞክሮም ይህንን አያሳይም፡፡ ይሁን እንጂ ከለውጡ በኋላ መንግሥት ጉዳዩን በመገንዘብ ዳያስፖራው ባንክ እንዲያቋቁም፣ ማክሮ ፋይናንስ እንዲያቋቁም፣ የመድን ድርጅት እንዲያቋቁም መፍቀዱ እንደ በጎ ጅምር ሊወሰድ ይችላል፡፡ በእኔ እምነት ከሁሉም በላይ ለዳያስፖራው ትልቁ ዋስትና የአገሩ ጉዳይ በመሆኑ፣ የተፈጠረውን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ መንግሥት የጀመረውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በተለይ በባንክ ኢንዱስትሪው ዘርፍ ማሻሻያ አጠናክሮ ኢንደሚቀጥል የሚጠበቅ ሲሆን፣ ዳያስፖራውን ለማገዝ የሚያስችል የዳያስፖራ ኤጀንሲ አቋቁሟል፡፡ በሠለጠነው ዓለም የሚኖረው ዳያስፖራም በማኅበሩ በኩል በመደራጀት የኢኮኖሚ ፍትሐዊነትና ነፃነት እንዲኖር የበኩሉን አስተዋፅኦ ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ቁጥር አንድ አጀንዳ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– ዳያስፖራው ከ70 በመቶ በላይ ባለድርሻ በሚሆንበት በዚህ ባንክ በዶላር አክሲዮን ገዝቶ የትርፍ ድርሻ ክፍያ የሚያገኘው ግን በብር መሆኑ፣ ምን ያህል ተቀባይነት ይኖረዋል?
አቶ ጋሻው፡– ከባንኩ ራዕይ፣ ተልዕኮና ዓላማ አንፃር የሚመሠረተው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ባንክ ዳያስፖራውን የአገሩ የኢኮኖሚ ልማት ዓርማና ምልክት እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ በዋናነት ዳያስፖራው በአገሩ የኢኮኖሚ ዕድገትና ልማት ላይ ከፍተኛ ድርሻ እንዲኖረው፣ በትልልቅ የኢኮኖሚ ዘርፎች ከኢትዮጵያዊያን ባለሀብቶች ጋር በመቀናጀት እንዲሠራና ቀጥተኛ የኢንቨስትመንት ተሳታፊ እንዲሆን ለማድረግ ያግዘዋል፡፡ ለዚህ ነው ባንኩ መካከለኛና ከፍተኛ ገቢ ባላቸው ባለሀብቶች ላይ ያተኮረው፡፡ ይሁን እንጂ ከኢኮኖሚ ፍትሐዊነትና አሁን ካለው የጥቁር ገበያ ችግር አንፃር ውስንነቶች እንደሚኖሩ፣ ከተለያዩ ክፍለ ዓለማት ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የተወሰደ ጠቋሚ መረጃ አመልክቷል፡፡ በዚህ ረገድ አዋጅ መውጣቱና ዳያስፖራውን የባንክ ባለቤት ማድረጉ ትልቅ ጅምርና የለውጡ አካል ተደርጎ መወሰድ እንዳለበት እናምናለን፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትም የባንክ ኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማዘመን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የማክሮ ኢኮኖሚ፣ በዋናነት የሞኒተሪ ፖሊሲ ማሻሻያ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡
ሪፖርተር፡– የባንክ አገልግሎቱ በመካከለኛና በከፍተኛ የኢኮኖሚ አውታሮች ላይ ያተኩራል ሲባል፣ ዳያስፖራው በተጨባጭ የሚያገኘው አገልግሎት ምንድነው?
አቶ ጋሻው፡– ከሁሉም በላይ የባንኩ ዓላማ ዳያስፖራውን በራሱ ስም የሚጠራ የባንክ ባለቤት እንዲሆን ማስቻል ሲሆን፣ ዳያስፖራው በሒደት መሠረተ ሰፊና ከፍተኛ በሆኑ የኢንዱስትሪ ዘርፎች በአነስተኛ የወለድ ምጣኔ ኢንቨስት እንዲያደርግ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ በዚህ ረገድ የሚሰበሰበውን 70 በመቶ የውጭ ምንዛሪ ባንኩ እንዲጠቀምበት በሕግ የተፈቀደ በመሆኑ፣ ትርፋማ በሆኑ የኢኮኖሚ ዘርፎች እንዲሰማራ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡
ሪፖርተር፡– በባንክ ኢንዱስትሪው ውስጥ በዚህ መንገድ መንቀሳቀስ የልማት ባንክ ባህሪ የሚያላብሰው ስለሚሆን፣ ከዚህ አኳያ የሚሰጣቸውን ብድሮች በምን ያህል ጊዜ ውስጥ ተመላሽ ያደርጋል?
አቶ ጋሻው፡– ባንኩ ከብሔራዊ ባንክ በተሰጠው ቅድመ ዕውቅና መሠረት የአክሲዮን ሽያጭ ከማስኬድ ጎን ለጎን፣ የዓለም አቀፍ የባንክ ኢንዱስትሪ አማካሪዎችን በመቅጠር ዝርዝር የአዋጭነት ጥናት በማስጠናት በሚያዘጋጀው የኮርፖሬት ፖሊሲና ስትራቴጂ በኩል የሚመለስ ሲሆን፣ ቀደም ሲል በተካሄደው ጠቋሚ ጥናት ግን ባንኩ እንደ ኢኮኖሚ ዘርፎች የአወቃቀር ባህሪይ፣ እንደ አገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገትና የልማት ደረጃ፣ እንዲሁም ባንኩ እንደሚሰበስበው የካፒታል መጠን የአጭር፣ የመካከለኛና የረዥም ጊዜ ብደር ይሰጣል ተብሎ ይገመታል፡፡
ሪፖርተር፡– የባንኩ ደንበኞች ወይም ተበዳሪዎች የትኞቹ የኅብረተሰብ ክፍሎች ናቸው?
አቶ ጋሻው፡– ቀደም ብሎ በተጠናው ጠቋሚ ጥናት መሠረት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ አራት አማራጮች ለይተን ለማየት ሞክረናል፡፡ በዚህ ረገድ የመጀመሪያው አማራጭ አነስተኛና ጥቃቅን ዘርፉ የሚገኝበት ዘርፍ ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ መካለከኛው ሲሆን፣ ሦስተኛው ከፍተኛውና ትልልቅ የኢኮኖሚ አውታሮች የሚሳተፉበት ነው፡፡ አራተኛው አማራጭ ግን የመካከለኛውና የከፍተኛው ውህድ ነው፡፡ ይህንን ውህድ በመውሰድ መንቀሳቀስ ለባንኩ የተለየ የእንቅስቃሴ ዘርፍ ሆኖ በመመረጡ፣ ይኼኛው አማራጭ የተሻለ እንደሚሆን በጥናቱ ተመልክቷል፡፡ በመሆኑም ከኢኮኖሚው አወቃቀርና ክፍፍል፣ እንዲሁም ከተነሳንበት የስፔሻላይዜሽን መርህ አንፃር ባንኩ በአብዛኛው መካከለኛውንና ከፍተኛውን ባለሀብት ይመለከታል፡፡ ይሁን እንጂ በአማራጭ ሞዴሉ መሠረት በገበያ ፍላጎትና አቅርቦት ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚሠራ ባንክ ይሆናል፡፡
ሪፖርተር፡– በሕዝብ መዋጮ አክሲዮን ያሰባሰበ ባንክ አገልግሎቱ በመካከለኛና በትልልቅ ኩባንያዎችና ባለሀብቶች ላይ ብቻ ያተኩራል ማለት ይችላል?
አቶ ጋሻው፡– በመርህ ደረጃ ባንኩ በአገር አቀፍ ደረጃ የኢኮኖሚ ነፃነትና እኩል ተጠቃሚነት፣ በዋናነት የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚው ውስጥ የሚኖረው ድርሻና ተሳትፎ ከፍተኛ እንዲሆን፣ የመወዳደሪያ ሜዳውም እኩል እኩል መሆን እንዳለበት ያምናል፡፡ በመሆኑም ባንኩ ከተነሳበት ራዕይ፣ ተልዕኮና ዓላማ አንፃር አገልግሎቱን ለነፃ ገበያ ክፍት በማድረግ በገበያ ተዋንያን የሚሰጠው አገልግሎትም ባስቀመጠው ሞዴል በአቅርቦትና በፍላጎት ላይ ይሠራል፡፡ ነገር ግን ከስፔሻላይዜሽን አኳያ በተመረጡ ዘርፎች የሚሠራ ሲሆን፣ በሩ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ክፍት ነው፡፡ ከኢኮኖሚ ትስስር አንፃር መሠረተ ሰፊ በሆኑ አዋጭ የኢኮኖሚ ዘርፎች በማተኮር የሥራ ዕድል በመፍጠርና የታክስ ገቢ በማመንጨት፣ በኢኮኖሚ የትስስር ሒደት ዝቅተኛው የኅብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ እንዲሆን ጥረት ይደረጋል፡፡
ሪፖርተር፡– ባንኩ በምን ያህል ጊዜ ውስጥ ሊመሠረት ይችላል?
አቶ ጋሻው፡– በታቀደው የካፒታል መጠን ወይም ሊመዘገብ በታቀደው የአክሲዮን ዋጋ ሽያጭ ፍጥነት ሒደት የሚወሰን ቢሆንም፣ በፕሮጀክት ዕቅዱ ሁለት ዓመት እንደሚሆን ተመልክቷል፡፡ በፕሮጀክቱ ፍኖተ ካርታ መሠረት የታቀደውን ግብ ከማሳካት አንፃር በዓለም አቀፍ፣ በአኅጉር አቀፍና በአገር አቀፍ ደረጃ በሚደረጉ የፕሮሞሽንና የማርኬቲንግ ሥራዎች አፈጻጸም የሚወሰን ይሆናል፡፡ የኩባንያው የካፒታል መጠን ስድስት ቢሊዮን ብር ነው፡፡ ከዚህ በላይ የተጠቀሰው ካፒታል እያንዳንዳቸው 20 ሺሕ ብር ዋጋ ባላቸው 300 ሺሕ ተራና የተመዘገቡ አክሲዮኖች የተከፋፈለ ነው፡፡ ዝቅተኛ የአክስዮን ብዛት አሥር ወይም 200,000 ብር ይሆናል፡፡ ማንኛውም ባለአክሲዮን ቢያንስ የካፒታሉን 60 በመቶ በቅድሚያ መክፈል፣ እንዲሁም ለሥራ ማስኬጃ የአገልግሎት ክፍያ አምስት በመቶ መክፈል ይጠበቅበታል፡፡
ኩባንያው በሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ ኤጀንሲ በተመዘገበ በ24 ወራት ውስጥ በሁለት ጊዜ ክፍያ ይጠናቀቃል፡፡ አክሲዮን የሚሸጥላቸው የውጭ ዜግነት ያላቸው ትውልደ ኢትዮጵያዊያንና ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያዊያን የሆኑ ባለሀብቶች በጋራ፣ ትውልድ ኢትዮጵያዊ የውጭ አገር ዜግነት ያለቸው ግለሰቦች ወይም የውጭ ዜግነት ያላቸው ትውልደ ኢትዮጵያዊያንና ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያዊያን ባለቤትነት ለተቋቋሙ ድርጅቶች ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ እያንዳንዳቸው 20,000 ብር የሚያወጡ 300,000 አክሲዮኖች፣ በጠቅላላው ስድስት ቢሊዮን ብር የሚያወጡ አክሲዮኖች ለሽያጭ ቀርበዋል፡፡ ሆኖም ኩባንያው በአጭር፣ በመካከለኛና በረዥም ጊዜ የባንክ አገልግሎት ሥራዎች ላይ እንደሚሰማራ በመታቀዱ፣ በብሔራዊ ባንክ መመርያ መሠረት ጠንካራ ጅማሮ እንዲኖረው ሲባል የተከፈለ ካፒታሉ አራት ቢሊዮን ብር ይሆናል፡፡