የምርጫ ክልሎች ካርታ ሰሞኑን ይፋ ይደረጋል
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የመራጮች ትምህርት መስጠት ለሚፈልጉ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጥሪ አደረገ፡፡ ቦርዱ ጥሪውን ያቀረበው ዜጎች በምርጫ ላይ ያላቸውን ትርጉም ያለው ተሳትፎ ለማረጋጋጥና ተዓማኒነት ያተረፈ ሰላማዊ ምርጫ ለማድረግ፣ የመራጮች ትምህርት አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
ይህንን ዓላማ በአገር ደረጃ ለማሳካት የሲቪል ማኅበረሰብ ተሳትፎ ትልቅ ሥፍራ እንደሚይዝ ቦርዱ ባወጣው መግለጫ አስረድቷል፡፡
ምርጫ ቦርድ በአገሪቱ ሕገ መንግሥትና በቦርዱ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 1133/2011 በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የመራጮች ትምህርት ለሚሰጡ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ የመስጠትና የመከታተል ኃላፊነቱን ለመወጣት የሚያስችለውን መመርያ በማርቀቅ፣ እንዲሁም በጉዳዩ ላይ ከሲቪል ማኅበራት ወኪሎች ጋር ባደረገው ውይይት ያገኘውን ግብዓት በማካተት የመራጮች ትምህርት ፈቃድ አሰጣጥና የሥነ ምግባር መመርያ ቁጥር 04/2012 ማፅደቁን አስታውሷል፡፡
በመሆኑም ለመራጮች ትምህርት መስጠት የሚፈልጉ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ማመልከቻ እንዲያቀርቡ ጥሪ በማድረግ፣ ትምህርቱን ለመስጠት ብቃት ላላቸው ማኅበራት ፈቃድ ሰጥቶ ማሰማራት አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን ጠቁሟል፡፡
በዚህ መሠረት በሕግ ተመዝግበው የሚንቀሳቀሱ፣ የማስተማሩን ተግባር ለመወጣት የሚያስችል ብቃት ያላቸው፣ ከማንኛውም የፖለቲካ ወገንተኝነት ገለልተኛ የሆኑ፣ ለመራጮች ትምህርት በመመርያው የወጣውን መሥፈርት የሚያሟሉና በተለያየ ሁኔታ የመራጮች ትምህርት ለመስጠት የሚፈልጉ አገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በቦርዱ በዝርዝር የሚጠይቋቸውን አግባብ ያላቸው ሰነዶችን በማያያዝ፣ ማመልከቻውን ለዋናው መሥሪያ ቤት ወይም ለቦርዱ የክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች ማስታወቂያ በመገናኛ ብዙኃን ከወጣበት ቀን ጀምሮ በአሥር ቀናት ውስጥ እንዲያቀርቡ ቦርዱ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሎች ካርታ ዝግጅት ያጠናቀቀ መሆኑን በማስታወቅ፣ ካርታው ይፋ የሚደረገው ግን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በተገኙበት እንደሆነ ገልጿል፡፡ በጉዳዩ ላይ ባለሙያዎችም ማብራሪያ ስለሚሰጡበት ቅዳሜ መጋቢት 5 ቀን 2012 ዓ.ም. የሚመለከታቸው አካላት በተገኙበት ይፋ የሚደረግ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በምርጫው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት የምርጫ ክልሎች ካርታ ይፋ የማድረጊያው ቀን ሰኞ መጋቢት 1 ቀን 2012 ዓ.ም እንደነበረ ይታወቃል፡፡