የኮሮና ቫይረስ በኢትዮጵያ በአምስት ሰዎች ላይ መገኘቱ ከተረጋገጠ በኋላ መነካካት ቫይረሱ ከሚስፋፋባቸው መንገዶች አንዱ በመሆኑ፣ የመንግሥትና የግል ተቋማት ሠራተኞች የጣት አሻራ እንዲቀርና የእጅ ፊርማ እንዲሆንላቸው እየጠየቁ መሆኑ ታወቀ፡፡
የገቢዎች ሚኒስቴርና በርከት ያሉ የግል ተቋማት ከሰኞ መጋቢት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ፣ የጣት አሻራ በማቆም የእጅ ፊርማ መጀመራቸውን ይፋ ማድረጋቸው ይታወቃል፡፡ ሌሎች በመንግሥትም ሆነ በግል ተቋማት የሚሠሩ ሠራተኞች ወረርሽኙ እስከሚወገድ ድረስ የጣት አሻራ ፊርማ ቀርቶ በእጅ ፊርማ እንዲሆንላቸው የጠየቁ ቢሆንም፣ ከተቋማቱ ኃላፊዎች ተግዳሮት እየገጠማቸው መሆኑን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ስማቸውንም ሆነ የተቋማቸውን ስም ቢገልጹ ገጽታ ማበላሸት መሆኑን የሚናገሩት ሠራተኞቹ፣ የጣት አሻራም ሆነ የእጅ ፊርማ ጠቀሜታቸው ሠራተኞች በመደበኛ የሥራ ሰዓት መግባትና መውጣታቸውን ማረጋገጥ ነው ይላሉ፡፡ የጣት አሻራ የአንድን ሠራተኛ ትክክለኛ መግቢያና መውጫ ሰዓታት የሚያመለክት ከመሆኑ አንፃር ተመራጭ ቢሆንም፣ ይህንን ቫይረስ መቆጣጠር እስከሚቻል ድረስ ማሽኑ በጣት የሚነካ ስለሆነ ድንገት ቫይረሱ ያለበት ሠራተኛ ቢነካው በርካታ ሠራተኞችን ሊጎዳ እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡ ጉዳቱ የሠራተኞች ብቻ ሳይሆን የተቋሙም ስለሚሆን ሊታሰብበት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡
መንግሥት ለቫይረሱ መስፋፋት ልዩ ትኩረት በመስጠት፣ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት እንዳይሄዱ ትምህርት ቤቶችን የዘጋው፣ በትምህርት ቤትም ሆነ በሚጓጓዙበት ወቅት በሚያደርጉት ንክኪ ቫይረሱን ወደ ቤተሰቦቻቸው ይዘው እንዳይሄዱ በማሰብ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የሚሠሩባቸው ተቋማት ለምን ሊያስቡላቸው እንዳልቻሉና ቀድሞ ለዓመታት ይታወቅ የነበረን አሠራር ለተወሰነ ጊዜ መጠቀም ለምን እንዳልተፈለገ እንዳልገባቸው ተናግረዋል፡፡
ምንም ይሁን ምንም የሚሠሩት ለመኖር በመሆኑ በቀላሉ መከላከል የሚቻልን ነገር እንዳይከላከሉ የሚገደዱ ከሆነ ሥራቸውን እስከ ማቆም እንደሚደርሱ ጠቁመው፣ ተቋማት የጣት አሻራን በፊርማ እንዲቀይሩላቸው ጠይቀዋል፡፡
የገቢዎች ሚኒስቴር ሠራተኞቹ የጣት አሻራን ትተው በእጅ ፊርማ እንዲጠቀሙ፣ ለቫይረሱ መከላከያነት የሚያግዙ ግብዓቶች ለሠራተኞቹ በቅርበት እንዲቀመጡላቸው፣ ግብር ከፍዮችም ሲመዘገቡ አሻራ ከመስጠታቸው በፊትና ከሰጡ በኋላ ፀረ ተህዋስያን ማፅጃን እንዲጠቀሙ የሚያስችል አሠራር ዘርግቶ፣ ከሰኞ ከመጋቢት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ አድርጓል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ሌላ ጥያቄ እያነሱ ነው፡፡ ይህም አንድ በኮሮና ቫይረስ የተጠረጠረ ግለሰብ በማግለያ ስለሚቆይበት ሁኔታ ነው፡፡ ነዋሪዎቹ እንዳስረዱት አንድ ሰው ሌላም ጊዜ እንደሚያጋጥመው የራስ ምታት፣ የምግብ አለመስማማትና ሌሎችም ሕመሞች ሲሰሙት የሙቀት መጠኑ ከፍ ሊል ይችላል፡፡
ይህ ሰው ሕክምና ለማግኘት ወደ ጤና ጣቢያዎች ሄዶ በሚደረግለት የሙቀት ልኬት ሙቀቱ ከፍ ቢል ሊገለል ስለሚችል፣ አለመሄድን እንደሚመርጥ ተናግረዋል፡፡ ይህ ደግሞ በቀላል ሕክምና ሊድን የሚችል ሕመም እስከ ሞት ሊያደርስ ስለሚችል፣ ኮሮና ቫይረስና ሌሎች ሕመሞች የሚለዩበት አሠራር እንዲኖር ጠይቀዋል፡፡