የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሎችን የሚያሳይ የመጀመርያውን የምርጫ ክልሎች ካርታ ይፋ አደረገ፡፡ ቦርዱ ይህን በዓይነቱ የመጀመርያው የምርጫ ክልሎች ካርታ ይፋ ያደረገው ቅዳሜ መጋቢት 5 ቀን 2012 ዓ.ም. ነው፡፡
የምርጫ ክልል ካርታው ይፋ በተደረገበት መድረክ ላይ የምርጫ ክልል ምንነትና አከላለል፣ እንዲሁም ከዚህ ቀደም የነበረውን የአከላለል ሕጋዊ ማዕቀፍ አስመልክቶ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና የሲቪል ማኅበራት ተወካዮች በተገኙበት በቦርዱ ኃላፊዎች ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
በዚህም መሠረት በዕለቱ 547 የምርጫ ክልሎችን ያካተተው የምርጫ ክልሎች ካርታ ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ መቀመጫ ይስተካከል የሚሉ ጥያቄዎች ለቦርዱ ይቀርቡ ስለነበር ጥያቄዎቹ እንዴት እንደተስተናገዱ ማብራሪያ ተጠይቋል፡፡
በዚህም መሠረት ካለው የጊዜ ገደብ፣ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ካለመከናወኑና እንዲሁም በሌሎች ተያያዥ ምክንያቶች የተጠየቁት ማስተካከያዎች እንዳልተከናወኑ የቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ገልጸዋል፡፡
በዚህም መሠረት ኦሮሚያ 178፣ አማራ 138፣ ትግራይ 38፣ አፋር 8፣ ሶማሌ 23፣ ቤኒሻንጉል ጉምዝ 9፣ ደቡብ 123፣ ጋምቤላ 3፣ ሐረሪ 2፣ ድሬዳዋ 2፣ እንዲሁም አዲስ አበባ 23 መቀመጫዎች ለፌዴራል ምክር ቤት እንደሚኖራቸው ተገልጿል፡፡
ቦርዱ መጪው ጠቅላላ ምርጫ ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. እንደሚካሄድ ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ በዚህም መሠረት ምርጫውን ለማከናወን ያስችሉኛል ያላቸውን የተለያዩ ሥራዎች በማከናወን ላይ እንደሚገኝ በወቅቱ ተገልጿል፡፡